Hiber Radio: በሽብር የተከሰሰው ወጣት በቅሊንጦ ማረሚያ ቤት ህክምና ተከልክሎ እንደሞተ ተገለፀ፣‹‹አውቀው ነው የገደሉት፡፡ እኛንም ይገድሉናል!›› 1ኛ ተከሳሽ መልካሙ ክንፈ

(በጌታቸው ሺፈራው)

በእነ መልካሙ ክንፈ የክስ መዝገብ በሽብር ተከሶ ቂሊንጦ እስር ቤት ታስሮ የነበረው ወጣት አየለ በየነ ነገሰ ህክምና እንዳያገኝ ተከልክሎ እንደሞተ ተገለፀ፡፡ ወጣት አየለ በየነ ህክምና ተከልክሎ ለሞት እንደተዳረገ በአባሪነት የተከሱት ዛሬ ሀምሌ 18/2009 ዓ.ም ለከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4 ወንጀል ችሎት ገልፀዋል፡፡

ተከሳሾቹ የፀረ ሽብር አዋጁ ከሚፈቅደው አራት ወር በተጨማሪ 5 ወር በአጠቃላይ 9 ወራትን ማዕከላዊ ታስረው እንደቆዩ የተገለፀ ሲሆን ሟች ለረዥም ጊዜ ታሞ ህክምና ቢጠይቅም ህክምና ሳይገኝ ቀርቷል ተብሏል፡፡ ህመሙ ከጠናበት በኋላም ከ10 ቀን በላይ ምግብ መብላት ባለመቻሉ ለእስር ቤቱ አስተዳደሮች በቀን ከሶስት ጊዜ ባላይ ህክምና እንዲያገኝ ጥያቄ ቢያቀርቡም መልስ ሳያገኙ መቅረታቸውንና በመጨረሻ ከእስር ቤቱ ውጭ እንዲታከም ቢታዘዝለትም በተቋሙ ቶሎ ህክምና ማግኘት ባለመቻሉ ህይወቱ ማለፉን ተከሳሾቹ ለፍርድ ቤቱ ገልፀዋል፡፡

ቀሪዎቹ ተከሳሾችም ህክምና ሊያገኙ ባለመቻላቸው ለህይወታቸው እንደሚሰጉ ለፍርድ ቤቱ አቤቱታቸው አሰምተዋል፡፡ 1ኛ ተከሳሽ መልካሙ ክንፈ ታሞ በየወሩ ህክምና እየወሰደ የነበር ቢሆንም መርማሪዎች የፈለጉትን መረጃ ስላልስጠ ህክምና መከልከሉንና የሟች እጣፈንታ ሊደርስበት እንደሚችል ስጋቱን ለፍርድ ቤት ገልፆአል፡፡ ‹‹አውቀው ነው የገደሉት፡፡ እኛንም ይገድሉናል፡፡›› ያለው 1ኛ ተከሳሽ ንፁህ በመሆናቸውና መረጃ ስላልተገኘባቸው ህጉ ከሚፈቅደው ውጭ ለ9 ወራት ማዕከላዊ መቆየታቸው ይህም ለንፁህነታቸው ማስረጃ እንደሆነ ገልፆአል፡፡ ማች ንፁህ በመሆኑም ክሱ እንዳይቋረጥ፣ ምስክሮችም ተሰምተው የፍርዱን ሂደት ማወቅ እንደሚፈልጉ ገልጾአል፡፡

ሌሎች ተከሳሾም ተመሳሳይ ችግር እንደገጠማቸው የተገለፀ ሲሆን 4ኛ ተከሳሽ ይማም መሃመድ ‹‹ይህን የሚያደርገው መንግስት ከሆነ ቁርጡን አውቀነው እንሞታለን›› ሲል ገልፆአል፡፡ ‹‹አየለን ሞተ ማለት አልችልም፡፡ ተቀጠፈ ነው የምለው፡፡ የሞተው ዘመድ አጥቶ አይደለም፡፡ ጓደኛና ቤተሰብ አጥቶ አይደለም፡፡ የሞተው ህክምና የሚሰጠው አጥቶ ነው›› ሲልም አክሏል፡፡

ባለፉት ቀጠሮዎች ሟችን ፍርድ ቤት ሳያቀርብ የቀረውን ቂሊንጦ እስር ቤት ፍርድ ቤቱ ተከሳሹን የማያቀርብበትን ምክንያት እንዲገልፅ ወይንም ተከሳሹን እንዲያቀርብ በጻፈለት ትዕዛዝ መሰረት ሀምሌ 17/2009 ዓ.ም ተከሳሽ መሞቱን ቢገልጽም በምን ምክንያት እንደሞተ እንዳልገለፀ ፍርድ ቤቱ አስታውቋል፡፡ ፍርድ ቤቱም ቂሊንጦ ሟች በምን እንደሞተና ለሞቱ ማረጋገጫ ባልላከበት ሁኔታ ግለሰቡ መሞቱን እርግጠኛ መሆን ስለማይቻል እስር ቤቱ ለሀምሌ 26/2009 ዓ.ም ተከሳሹ ስለመሞቱ የሚያሳይ ማረጋገጫና የሞተበትን ምክንያት እንዲያመጣ ሲል ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

አየለ በየነ በመዝገቡ ስር 2ኛ ተከሳሽ የነበር ሲሆን ከኦነግ መሪ ዳውድ ኢብሳ ጋር ግንኙነት በመፍጠር እና ሀገር ውስጥ ያሉ መረጃዎችን ሪፖርት አድርጓል የሚል ክስ ቀርቦበት ነበር፡፡ የሟች ታናሽ ወንድም ቦንሳ በየነም በዚሁ ክስ መዝገብ ስር ክስ ተመስርቶበታል፡፡ በመዝገቡ ስር፡-

1.መልካሙ ክንፉ ተፈሪ

2. አየለ በየነ ነገሰ

3. ቦንሳ በየነ ነገሰ

4. ይማም መሃመድ ኬሮ

5. ለሜሳ ግዛቸው አባተ

6. ኩመራ ጥላሁን ዴሬሳ

7. መያድ አያና አቶምሳ

8. ሙሉና ዳርጌ ሩዳ የተከሰሱ ሲሆን ተመሳሳይ ችግር እየደረሰባቸው እንደሆነ ተገልፆአል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ የቀድሞ በስልጣን ላይ አለው የሕወሓት/ኢህአዴግ አገዛዝ የደህነት ሹም የነበሩት አቶ አያሌው መንገሻ ከህብር ሬዲዮ ከዚህ ቀደም ባደረጉት ቃለ መጠይቅ በፖለቲካ ጉዳይ የታሰሩ እስረኞች ህክምና እንዳያገኙ ካገኙም የውሻ መግደያ መርዝ ጭምር እንደሚወጉ መግለጻቸው ይታወሳል።

ከአቶ አያሌው መንገሻ ጋር አድርገነው የነበረውን ቃለ መጠይቅ ለትውስታ አያይዘነዋል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *