Hiber Radio: የማያባራውን ስርዓት ወለድ የእልቂት ዘመቻ በህብረት እንቅረፈው! ትኩረት የሚሻው የዶ/ር አክሎግ ቢራራ ወቅታዊ ትንታኔ

አክሎግ ቢራራ(ዶ/ር)

እረጋ ብለን ብናጤነው፤ እኛ ኢትዮጵያዊያን ከሚለያዩን ሁኔታዎች በላቀ ደረጃ የምንጋራቸው ጥሪቶች፤ የታሪክ ሂደቶች፤ ልምዶች፤ የጋራ መነሻዎችና ብናውቅበት፤ የጋራ መድረሻዎች አሉን። ብናውቅበት፤ የተፈጥሮ ኃብታችን ለአገራችን ሕዝብ ፍላጎት ይበቃል፤ ለሌችም ሊተርፍ ይችላል። በዚህ ወር ብቻ ኢትዮጵያ በዓለም ደረጃ ከፍተኛ ገቢ የሚያስገኝ የወርቅ ኃብት ሊመረትባት የምትችል አገር መሆኗ በሰፊው ተወርቷል። የውሃ ኃብቷ ዝነኛና አኩሪ መሆኑ ከተወራ ቆይቷል። የተፈጥሮ ኃብት እርግማን ወይንም ምርቃን ሊሆን ይችላል። ጥያቄው፤ እነዚህንና ሌሎችን የተፈጥሮ ኃብቶች ማን ይጠቀምባቸው ይሆን? የሚለው ነው።

ቢያንስ ቢያንስ፤ የኢትዮጵያ ህጻናት በቋንቋና በጎሳ ልዩነቶች ላይ በተመሰረተው የህወሕት/ኢህአዴግ አገዛዝ ሊጨፈጨፉ አይገባም ነበር;፡ እነዚህ ለጋውዎችና ጮርቃዎች ምን ወንጀል ሰርተው ነው በዚህ አገዛዝ በተደጋጋሚ፤ በጭካኔና ታይቶና ተሰምቶ በማይታወቅ ደረጃ የሚጨፈጨፉት? በቆቦ የሰባት ዓመት ልጅ፤ በወልድያ የአስራ ሶስት ዓመት ወጣት፤ ቀደም ሲል በቡኖ በደሌ የሶስት ወር ህጻን ሴት ልጅ ተረሸነች፤ የስድስት ወር ሕጻን ሴት ልጅ ወደ ጉድጓድ ተወርውራ ተገደለች። ይህን ጭካኔ የሚፈጽመው የህወሓት አጋዚና በህወሓት የሚመሩ የፌደራልና ሌሎች ኃሎች ናቸው። ከመቀሌ የበረረው “የትግራይ”  ሄሊኮፕተር በንጹሃን አማራዎች ላይ ጭካኔ ሲፈጽም ከዚህ የባሰ የዘር ማጥፋት ዘመቻ ሊጠበቅ አይችልም። የተቀነባበረው የአማራን ብሄር የማጥፋት እርምጃው ዛሬ ሳይሆን የተጀመረው ህወሓት ሥልጣን ከመያዙ በፊት ነው—ወልቃይት-ጠገዴ። የአማራው ብሄር ተተኪ መሪዎችና ተተኪ ትውልድ እንዳይኖረው የአማራ ህጻናትም ጭምር እየተጨፈጨፉ ነው።

ይህ በቋንቋና በጎሳ ለይቶ ህጻናትን ጭምር የመረሸን በሽታ ከየትና ለምን ተከሰተ? የሚለውን፤ እርህራሄ የሌለው የተደጋገመ ወንጀል መጠየቅና ለዚህ ኢ-ስብአዊ ወንጀል መፍትሄ መፈለግ ያለበት ለሂሊኖው የሚገዛ ግለሰብ ሁሉ ነው። በመጀመሪያ ደረጃ ራሱን ከዚህ እልቂት ማዳን ያለበት አማራውና ኦሮሞው ነው።ኢትዮጵያ ህጻናቶቿንና ሌሎች ልጆቿን እያስጨፈጨፈች ልትቀጥል አትችልም። የህወሓት ኢላማ የሆነው የኦሮሞውን የአማራው ሕዝብ በተለይ፤ ራሱን ከጭፍጨፋና ከውርደት ለማዳን ቆርጦና ተባብሮ ጨካኙን የህወሓትን ነፍሰ-ገዳይ ቡድን በጋራ መታገል አለበት። ይህ ግዙፍና እምቅ ኃይል ያለው ሕዝብ፤ ከአሁን በኋላ ህወሕት ህጻናትን እንዲጨፈጭፍና ኢትዮጵያን እንዲገዛ መፍቀድ የለበትም።

ከላይ ተገኘ የተባለው የወርቅ ኃብትና ሌሎች ግዙፍ የተፈጥሮ ኃብቶች፤ ለህወሓቶችና ለሌሎች ኪራይ ሰብሳቢዎች ሳይሆን፤  ለአገርና ለዜጎች ጥቅም ከዋሉ፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከድህነት ሰቆቃ ነጻ እንደሚወጣ አልጠራጠርም። ኢትዮጵያ ከውጭ እርዳታ ነጻ ወጥታ ኃብታምና ጠንካራ አገር ልትሆን ትችላለች። ይኼ ስኬታማ ሊሆን የሚችለው ግን ጭፍጨፋው በአስቸኳይ ሲቆም፤ ወንጀለኞቹ ለፍርድ ሲቀርቡ፤ ብሄራዊ መግባባት ሲኖርና ሕዝቡ የፖለቲካ ሥልጣኑ ባለቤት ሲሆን ነው። ሕዝብ የፖለቲካ ሥልጣኑ ባለቤት የሚሆነው በምኞት አይደለም። በፖለቲካ ልሂቃን ጥረት ብቻ ሊሆንም አይችልም። ሕዝብ የፖለቲካ ሥልጣኑ ባለቤት የሚሆነው እውነተኛ ዲሞክራሳዊ ሥር ዓት ሲመሰረት ብቻ ነው።

እኛ የሚጎድለን ለጋራ አገር ክብርና ለአንድ ህብረ-ሕዝብ የጋራ ጥቅምና የፍላጎት ማሟላት ጥረት የጋራ ዓላማ አለመኖሩ፤ ጭካኔዎችን በጋራ ተታግለን ለማቆም አለመቻላችን ነው።አንዱ ሲጨፈጨፍ ሌላው በፍጥነት አለመነሳቱ ነው። ባለፉት ሃያ ሰባት ዓመታት በሚዘገንንና በሚጎዳ ሁኔታ የታየውና የተከሰተው እንደምታ፤ የራስን ወይንም የግልን ወይንም የብሄርን/የጎሳን ጥቅም ከአገርና ከሕዝብ ጥቅም በላይ መተግበራችን ነው። በቋንቋና በጎሳ ልዩነቶች ላይ የተመሰረተው ‘የፌደራል” አገዛዝ ለጋራ ብሄራዊ ዓላማ፤ ለአገር አንድነት፤ ሉዓላዊነትና ለጋራ የሕዝብ ኑሮ መሻሻል ጸር ሆኗል። የማንነት ጥያቄ በተሳሳተና አደገኛ በሆነ መንገድ እንዲተገበር ተደርጓል። ህጻናትን ለይቶ መግደል ከዚህ የማንነት ጥያቄ ጋር የተያያዘ ነው። የጋራ አገር የጋራን መብትን የጋራን ጥቅም ማስከበር አለበት። “ተባበሩ ውይንም ተሰባበሩ” ይላሉ አበው።

የማናኛውም ኢትዮጵያዊ የቋንቋ፤ የባህል፤ የኃይማኖት፤ የታሪክና ሌሎች መለያዎቹ ሕጋዊ እውቅና እንዲኖራቸውና እንዲከበሩ እፈልጋለሁ። በተመሳሳይ ደረጃ ዋናው የዜግነት መለያችን ኢትዮጵያዊነት ሕጋዊና ብሄራዊ ተቀዳሚነት እንዲኖረው ሁላችንም መረባረብ አለብን። የተጨፈጨፉትና በእስር ቤቶች የሚሰቃዩት ወንድሞቻችን፤ እህቶቻችን ዋናው መለያቸው ሰብእነታቸው፤ ኢትዮጵያዊነታቸው ነው። አማራው ኢትዮጵያዊ፤ ኦሮሞው ኢትዮጵያዊ፤ አኟኩ ኢትዮጵያዊ ወዘተ ተጨፍጭፏል፤ ይጨፈጨፋል። በተለየና በባሰ ደረጃ የሚጨፈጨፈው በኢትዮጵያዊነቱ የሚያምነውና የሚኮራው፤ ለሁሉም ኢትዮጵያዊያን የሚታገለው፤ ለዲሞክራሲና ለሕግ የበላይነት የሚከራከረው ክፍል አባል መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ።

ቁም ነገሩ ኦሮሞው ሆነ፤ አማራው፤ አኟኩ ሆነ ሌላው ሲጨፈጨፍ በአንድ ድምጽ፤ በአንድነት መቆም ወሳኝ መሆኑ ነው። ይህን አላደረግንም። የእያንዳዱ ኢትዮጵያዊ ሞት የራሳችን ሞት መሆኑን መቀበል ግዴታችን ነው።“የኦሮሞው ሞት የእኔም ሞት ነው፤ የአማራው ሞት የእኔም ሞት ነው” የምንልበት ጊዜ ዛሬ ነው። ይህ መፈክር መተግበር አለበት።

በማንነት ጥያቄ ዙሪያ የሚደረገው የፖለቲካ ንግድ ለኢትዮጵያ አደገኛ መሆኑን፤ ለሚደረገው እልቂት መንስኤና ምክንያት መሆኑን በተደጋጋሚ አይተናል፤ ተጨማሪ መረጃ አያስፍልገንም። በአንድ ድምጽ እልቂቱን ማውገዝና እልቂት እንዳይደገም ማድረግ ወሳኝ ሆኗል። ጭፍጨፋ የህወሓት ሥልጣን ማቆያ መሳሪያ እንዲሆን መፍቀድ የለብንም። እልቂት እየተካደ እድገት አለ፤ የውጭ መዋእለንዋይ “በሽ በሽ ነው” የሚሉ አፈቀላጢዎች እድገቱንና ፈሰሱን ከእልቂቱ ጋር አጣምረው ተናግረው አያውቁም። ፈሰሱ ለጥቂቶች መሳለቂያና መዝናኛ ከሆነ ማህበረሰባዊው ፋይዳው የት ላይ?ነው።

ለእኔ ገዢና ወሳኝ መመሪያየ ጎንደር መወለዴና የአማራ ብሄር አባል መሆኔ አይደለም። ይኼን ማንነቴን ማንም ኃይል ሊነጥቀኝ ወይንም ሊያስተምረኝ አይችልም። ዋናው መለያየ ኢትዮጵያዊነቴ ነው።ሰብእነቴ ነው። ጎንደሬው “የኦሮሞው ደም ደማችን ነው” ሲል እምነቴ በኢትዮጵያዊነቴ ነው ማለት ነው። ይህ የጋራ መለያችን ሊሰብስበን ይገባል።

እኔ ክልል (መለያ) የሚለውን የመለያያ ቃል አልቀበልም። መለያየት ስለሆነ። “የክልሉ” ስርዓት የኢትዮጵያን ዘላቂ ጥቅም ለማስከበር፤ ኢትዮጵያዊነትን ለማጠናከር፤ የዜጎችን የኑሮ ፍላጎት ለማሟላት፤ የኢትዮጵያዊያንን ትሥስር መሰረት ለማጠናከር አላስቻለም። “የክልል” ምሁራን፤ ልሂቃንና ሌሎች የጋራ ወይንም ኢትዮጵያዊ የሆነ ዓላማ አይጋሩም። ዛሬ አገራችን ለጥቃት ካጋለጧት እንደምታዎች መካከል አንዱ እኛ ኢትዮጵያዊያን ለጋራ አገር፤ ለጋርዮሽ ጥቅም በጋራ ለመወያየትና መፍትሄዎችን ለመፈለግ ፈቃደኛ አለሞሆናችን ነው። “እኔ ያልኩት ብቻ” የሚል የትእቢተኞች ብሂለ የትም አላደረሰንም፤ አያደርሰንም። ይህ በብሄርና በቡድን ዙሪያ መበታተን ለገዢው ፓርቲና ለውጭ ጠላቶች መሳሪያ ሆኗል።

ዛሬ፤ ለመሬትና ለሌላ የተፈጥሮ ኃብት የበላይነት የሚደረገው የጦፈ ትግል በብሄር ማንነትና ጥቅም ዙሪያ ሲሆን፤ ተጠቃሚው ተራው ሕዝብ ሳይሆን በአብዛኛው ጠባብ ብሄርተኞችና እነሱ የፈጠሯቸው ኪራይ ሰብሳቢዎች የሚባሉት ናቸው። የክልሉ ስርዓት ጠባብ ብሄርተኝነትን፤ የግል/የቤተስብንና የቡድንን ጥቅሞችአጠናክሯል፤ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን አዳክሟል። ለጭፍጨፋው መሰረታዊ ምክንያት ይኼ በጥቅም ዙርያ የተቀናጀ፤ “እኛና እነሱ” የሚል የማይታረቅ ልዩነት እየሆነ መሄዱ ያሳፍራል። “እኛ ኢትዮጵያዊያን” የሚለው ብሄራዊ መፈክር ለምን ተናቀ?

በማንነት ስም የግልና የቤተሰብ ጥቅም፤ የብሄርና የአካባቢ ጥቅም የበላይ በሚሆንበት ጊዜ ትግሉና ትኩረቱ ለጋራ ዓላማ ሊሆን አይችልም። የኢትዮጵያ የውጭ ጠላቶች እኛን የሚያጠቁን በራሳችን ስግብግብነት፤ በራሳችን ጉራ፤ በራሳችን አለመግባባት ወዘተ ነው። ኢትዮጵያዊነትን የዜግነት መለያችን አለማድረግ ለውጭ ጠላቶቻችንም መሳሪያ ነው።

ገዢው ቡድን ትላንት የኦሮሞውን ወጣት፤ ዛሬ የአማራውን ወጣት፤ ነገ የአኟኩን ወዘተ እየለየና እየከፋፈለ የሚጨፈጨፈው፤ በህወሓት የበላይነት የሚመራው አገዛዝ በምንም መስፈርት ቢገመገም፤ ራሱን ተችቶና አርሞ ለኢትዮጵያ ዘላቂነት፤ ለሕዝቧ፤ በተለይ ለወጣቱ ትውልድ ህይዎት ፋይዳ ያለው ለውጥ ያመጣል ብሎ መናገርና ማሰብ ሕዝብን ያስጠቃል፤ አገርን ያጠፋል። ህወሓት የሕዝብን መዋእለንዋይ ፈሰስ እያደረገ ራሱን እገመግማለሁ ሲል፤ መፍትሄ የሚፈልገው እንዴት አድርጌ የበላይነቴንና ስልጣኔን ልቀጥል በሚል ስልት እንጅ፤ ሕዝብ ስለጠላኝና ስለማይፈልገኝ፤ ስልጣኔን ለሕዝብ ላስረክብ፤ ሕዝቡ የፖለቲካ ስልጣኑ ባለቤት ይሁን፤ሕዝቡ የተፈጥሮ ኃብቱ ተጠቃሚ የመሆን መብት አለው በሚል እምነት አይደለም። ገዢው ቡድን የሚፈራው ሕዝቡን ነው። ሕዝቡን ከፈራው፤ እየለየ የሚገድለው ለሕዝቡ መብት የቆመውን ግለሰብ ነው። ይህ እየለዩ ማጥቃት አገር ውስጥና አገር ውጭ ያለውን አይለይም።

አገዛዙ ፍትህና ነጻነት ለሚፈልገውና በሰላም ድምጹን ለሚያሰማው ዜጋ ሁሉ የሚሰጠው መልስ አንድ ብቻ ነው–ጭካኔናግድያ። ይህ የማያባራ ጭካኔ ሊቆም የሚችለው አገዛዙ ተወግዶ ሕዝብ የፖለቲካ ሥልጣኑ ባለቤት ሲሆን ብቻ ነው። ሕዝብ የፖለቲካ ሥልጣኑ ባለቤት የሚሆነው ዲሞክራሳዊ ስርዓት ሲመሰረት ብቻ ነው።  “ዲሞክራሲን” መነገጃ ያደረገው፤የህወሓት ባህርይና ተልእኮ ይለወጣል ብሎ ማሰብ ራስን እየሸነገሉ፤ ሕዝብን ለእልቂት ማጋለጥ ነው። ሽንገላው በልዩ ልዩ መልኮች ይታያል። ለምሳሌ፤ ገዢው ቡድን “በኢትዮጵያ አንድም የፖለቲካ እስረኛ የለም” ካለ በኋላ ሁሉንም የፖለቲካ እስረኞች እፈታለሁ ብሎ ማለ፤ ተገዘተ። የታወቀውን የፍትህ፤ የነጻነትና የዲሞክራሲ ጠበቃ፤ ከጅምሩም መታሰር የሌለበትን ፕሮፌሰር መረራ ጉዲናን ፈታ።

ይህ ጥሩ ውሳኔ ነው። በመቶ የሚቆጠሩ የታሰሩበት ምክንያት ግልጽ ያልሆነ ዜጋዎችንም ፈታ። ሆኖም፤ በብዙ ሽህ የሚገመተውን፤ ከእነዚህ መካከል ዓለም የሚያውቃቸውን የፖለቲካ እስረኞች (እስክንድር ነጋን፤ አንዱዓለም አራጌን፤ አንዳርጋቸው ጽጌን ወዘተ፤ ወዘተ) አልፈታም። የኢትዮጵያንና የዓለምን ሕዝብ ለመሸንገል የተደረገው እርምጃ ትዝብትን አስከትሏል። ዛሬ ፈታሁ ብሎ ነገ ያስራል። የተባበሩት መንግሥታትና ሌሎች ዓለም አቀፍ ድርጅቶችና መንግሥታት “የኢትዮጵያ መንግሥት ያልተፈቱትን የፖለቲካና የህሊና እስረኞች በአስቸኳይ እንዲፈታ” የጠየቁበት ዋና ምክንያት ገዢው ቡድን በኢትዮጵያዊያን ህይወት መነገዱኑና መቀለዱን ስለቀጠለ ነው። ሁሉም የፖለቲካ እስረኞች እንዲፈቱ ተከታታይ ትግልና ጥረት ማድረግ ግዴታችን ነው።ከዚህ በበለጠ ግን አገር ቤት የሚታገሉትን ወገኖቻችን መደገፍ ወሳኝ ነው።

የታወቁ የፖለቲካ እስረኞችን የማይፈታበት ምክንያት ተቀናቃኝ ስለማይፈልግ ነው። ገዢው ቡድን ሰላምንና መግባባትን አይወድም።እንደራደር ሲል ማዘናጊያ ነው። ልዩነቶችን ማስተናገድን አይፈቅድም። ሌላው ቀርቶ ለኃይማኖትና ለእምነት ተከታዮች ደንታ የለውም።እንዲያውም ስለማያከብራቸው እያጠፋቸው ነው።

ህወሓት በበላይነት የሚያሽከረከረው አገዛዝ ማንኛውንም “ተቃዋሚ” አይምርም። በሰላም የሚታገል ግለሰብ፤ ልዩነቱን በሰላማዊ መንገድ ሲገልጽ አይምረውም። አንድ ኢትዮጵያዊ፤ ነጻነቱን መሰረት አድርጎ፤ “ሕገመንግሥቱ” የሚሰጠውን ሰብአዊ መብት ተጠቅሞ በሰላማዊ መንገድ ሃሳቡን በጽሁፍ ሆነ በአካል ቢገልጽ ልክ መሳሪያ ይዞ ከሚታገል ግለሰብ አይለየውም። ለገዢው ፓርቲ ተቃዋሚ ማለት “ጸረ-ሕገመንግሥት፤ ጸረ-ሰላምና እርጋታ፤ ጸረ-ዲሞክራሲ” ነው። መስፈፈርቱን ያወጣው ራሱ ነው፤ ትርጉሙን የሚሰጠን ራሱ ነው። ፈራጁ ራሱ ስለሆነ፤ በሰላም ተቃውሞውን የሚያሰማ ግለሰብ “ጠላት” ነው።ዲሞክራሲን አከብራለሁ በሚል ማባበያ ጸረ-ዲሞክራሳዊ ስራዎችን ሲተገብር የቆየን ቡድን ዛሬ፤ ነገ ይለወጣል ብሎ ማመን ራስን ማታለል ነው። በአጭሩ፤ በጠላትነት የተፈረጀ ስርዓት ዲሞክራሳዊ ሊሆን አይችልም።

የዚህ ትንተና መሰረታዊ ሃሳብ፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ እና “አማራጭ ኃይሎች” ከአሁን በኋላ እናቶች፤ በህወሓት የበላዮችና አለቃዎች አልሞ ተኳሽዎችና በሌሎች ለሕዝብ ህይወት ደንታ የሌላቸው ጨካኞች የሚገደሉትን ልጆቻቸውን እያለቀሱ ከመቅበር ባሻገር ዘላቂ መፍትሄ መፈለግ ታሪካዊ ግዴታችን ነው የሚል ሃሳብና ምክር ነው። “ነገ ባለተራው ማን ይሆን?” እያልን ሃያ ሰባት የስቃይ ዓመታትን አሳልፈናል።ከግል ጥቅምና ከግል ዝና ውጭ፤ ይህ ሊቀጥል አይችልም ብለን ለመነሳት የማያስችለን ሁኔታ የለም።ምክንያቱም፤ ገዢው ቡድን ጥቂት ግለሰቦችን ስለፈታ ይኼን እንደ መልካም እርምጃ የምናስተጋባ አለን። ገዢው ቡድን መልካም እርምጃ አካሂዷል ለማለት የምንችለው ሁሉም የፖለቲካ እስረኞች ሲፈቱ፤ ጭፍጨፋው ሲያቆምና የነጻነት ጮራ ሲታይ ነው። ማባበያውን እንደ መሰረታዊ ለውጥ ካስተጋባን ግንአቋማችን የሚያጠናክረው የገዢውን ፓርቲ እጅ ነው። የህወሓት አጋፋሪዎች የሚሰብኩት ሁሉም ነገር “አማን” እያሉ ነው።ህጻናትን እየጨፈጨፉና እያፈኑ አማን! እየሰረቁ አማን” የማታለያ መሳሪያ ነው።

ገዢው ቡድን አሁንም በመርሆዎች ይነግዳል። “ዲሞክራሲ” እየተስፋፋ ነው! እድገቱ በአዲስ “የተሃድሶ መርህ” ይቀጥላል ወዘተ፤ ወዘተ የሚለው ማሳሳቻ እንጅ ሃቁን በግልጽ የሚያቀርብ ትንተና አይደለም። የዲሞክራሲው ምህዳር እየጠበበ እንጅ እየተስፋፋ አልሄደም። አፈናው፤ ጭካኔውና ግድያው እየተባባሰ እንጅ እየተሻሻለ አልሄደም። ቢሻሻል ኖሮ “የወልድያው ጭፍጨፋ” አይካሄድም ነበር። የሰባት፤የዘጠኝ ዓመት ወጣት የሚገድለው ህወሓት ከፋሽስቶች በምን ይለያል? “ነብር ቆዳውን እንደማይቀይር ሁሉ” ህወሓት ርእዮቱን፤ ዓላማውንና ተልእኮውን አልቀየረም።

All Africa and Ethiopian Herald በየቀኑ የሚያቀርቡት ዘገባ ሰላምና እርጋታ እንዳለ፤ እደገቱ ሳያቋርጥ እንደሚካሄድ፤ የውጭ መዋእለንዋይ እንደቀጠለ፤ የውጭ ምንዛሬ ችግር እንደሌለ አድርገው ነው። እልቂት እንደሚካሄድ አይናገሩም።የእድገቱ ውጤት የዚህን ያክል የሚያኮራና ፍትሃዊ አለመሆኑን አያወሱም።

የህወሓት ርእዮት፤ ተልእኮና መመሪያ የብሄር ጥላቻንና የጥቂት የትግራይ ተወላጆችንና ታማኞችንየፖለቲካና የኢኮኖሚ የበላይነት የሚያስተናግድ የአመራር ስልት ነው። ለሰው ኑሮና ህይወት እርህራሄና ምህረት አያሳይም። እንዲያውም፤ በአገርና በሕዝብ ጥቅም ላይ አቋም በመውሰድ፤ ማንኛውንም ወቅትና እድል ተጠቅመው ሰላማዊ ድምጽ የሚያሰሙትን ግለሰቦች ሁሉ እየለየ በአልሞ ተኳሾች መግደሉን የማያቆም ቡድን መሆኑ በተደጋጋሚ ታይቷል። ወገንን ከወገን እየለየ፤ ሌሎችን እየተጠቀመና መሳሪያ እያደረገ አፈናውንና ማሳደዱን ቀጥሏል። የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን “የኢትዮጵያ ሁኔታ በጣም ያሳስበናል” ያለበት ዋና ምክንያት ጭካኔው ተቀባይነት እንደሌለውና በዓለም ሕግ እንደሚያስከስስ ስላመነበት ነው። ይህም የጋራ ጥረትን ይጠይቃል፤ መጮህ ብቻ በቂ አይደለም።

በዚህ በያዝነው የኢትዮጵያ አዲስ ዓመት በኦሮሞው ሕዝብ ላይ የተካሄደው ጭካኔ ዛሬ ደሞ በአማራው ሕዝብ ላይ ተካሂዷል። ሁለቱ የሕዝብ አካሎች ዋና ኢላማ መሆናቸው የሚቆም አይመስለኝም። የሚያዋጣው፤ ኦሮሞው፤ አማራውና ሌላው፤ ኢትዮጵያዊነቱን ተቀብሎና በአንድነት ሆኖ ጨካኙን አገዛዝ ማስወገድ ብቻ ነው። ህወሓት ራሱን በሰላም ይለውጣል ብሎ ማስተናገድ፤ ራስን ማታለልና ወጣቱን ትውልድ ለባሰ ተከታታይ እልቂት ማጋለጥ ነው።

በዚህ ትንተና፤ በመጀመሪያ፤ በወልድያ ንጹሃን ላይ፤ በተለይ በህጻናት ላይ የተደረገውን ጭፍጨፋ እኔም በዜግነቴ አወግዛለሁ፤ ያወገዙትን ሁሉ አደንቃለሁ። መስዋእት ለሆኑት “ሰማእታት” ቤተሰቦች ሁሉ ሃዘኔን እገልጻለሁ። በወልድያ ወጣት ወንድሞቻችን፤ በተለይ በህጻናት ላይ የተካሄደው እልቂት ታሪክ የመዘገበው፤ ምንም ይቅርታ የማይደረግበት እልቂት (Selective and deliberate ethnic genocide) ነው። በዓለም ፍርድ ቤት ክትትል ሊደረግበት የሚገባ ወንጀልነው እላለሁ። ግድያውን የፈጸሙት ባለሥልጣናትና ገዳዮቹ ለፍርድ እንዲቀርቡ እንረባረብ እላለሁ።

በዓልን ማክበርና ድምጽን ማሰማት መብት ነው

እኔ ስንት ሰው በእልቂት እስኪሞት ድረስ እያዘንን እንደምንቆይ አልገባኝም። ሕዝቡ ብሶቱና ጭካኔው ስላየለበት፤ ሞትን ንቆታል፤ ለመሞት ቆርጧል። መጥረቢያ ይዠ እዋጋለሁ እያለ ነው። የወልድያ ወጣቶች በቃና ዘገሊላ በዓል ሲያከብሩ፤ በህወሓት የበላይነት በሚታዘዘው ኃይል ሲጨፈጨፉ ከጀርባ ሆኖ ያስጨፈጨፋቸው ኃይል እንዳለ ማወቅ ይኖርብናል። ህወሓት የመሬት ነጠቃንና መስፋፋትን ከሚያካሂድባቸው አካባቢዎች መካከል አንዱ ወልድያ ነው። የመሬት ነጠቃና ጭካኔ አብረው የሚሄዱ መሆናቸውን ከዚህ በፊት ስለ ጋምቤላ፤ ስለወልቃይትና ስለ ሌሎች የመሬት ነጠቃዎች፤ የህወሓት መስፋፋቶችና የሕዝብ ፍልሰቶች ጉዳቶች በሚመለከቱ ጉዳዮች ላይ፤ በመረጃ የተደገፉ ትንተናዎችን አቅርቤአለሁ።

በኦሮሞው ሕዝብ ላይም የተካሄደው ጭፍጨፋ በተመሳሳይ የውስጥ ሴራና ትእዛዝ የተካሄደ ነው። ስለሆነም፤ አዛዡና ወንጀለኛው ማነው ብለን የመጠየቅ ግዴታ አለብን። በአማራውም ሆነ በኦሮሞው ክልል “ለሕዝብ ታዛዢዎችና ተገዢዎች ነን” የሚሉ የክልል ባለሥልጣናት ደፍረውና ቆርጠው ነፈሰ ገዳዮች በአስቸኳይ ለፍርድ ይቅረቡ የሚሉበት ወቅት አሁን ነው። ህወሓት በመሬቶቻቸው ላይ ሚና እንዳይኖረው ማድረግ ግድ ይላል። አለያ፤ እነሱም ከህወሓት ሊለዩ አይችሉም።

ልክ እንደ ኦሮሞ ወንድሞቻቸና እህቶቻቸው፤ የወልድያ ወጣቶች ድምጻቸውን፤ ጸሎታቸውን፤ አቤቱታቸውን ከማሰማት ባለፈ መንገድ ማንንም ድንጋይ ወርውረው አልጎዱም፤ የማንንም ንብረት አላወደሙም። የማንንም ብሄር አባል ኢላማ አላደረጉም። ሌላው ቀርቶ፤ በበዓል ቀን ድምጽንና ልዩነትን ማሰማት ወንጀል የሆነባት አገር ኢትዮጵያ መሆኗ በተደጋጋሚ ታይቷል። ነፍሰ ገዳዮችና ወንጀለኞች ለፍርድ ካልቀረቡ በስተቀር ሌላው ነገ ባለተራ መሆኑ አይቀርም።

አገዛዙ ካልተለወጠ ይህን የመሰለው ጭካኔና ግድያ ሊያቆም አይችልም የምልበት መሰረታዊ ምክንያት ጭካኔውና ግድያው የተጀመረው ዛሬ ስላልሆነ ነው። አፈናና ጭፍጨፋ የአገዛዙ ዋና መሳሪያዎች በመሆናቸው ነው። ከምርጫ ዘጠና ሰባት ውጭ፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ አንድም ቀን በሰላም አድሮ፤ በሰላም ድምጹንና መብቱን አስተላልፎና አስከብሮ አያውቅም። መሰረታዊ ለውጥ ወሳኝ ነው የምልበትም ምክንያት ይኼው ነው።

ወልድያ ከተማ የመንግሥት ታጣቂዎች ፈፅመውታል ያሉትን የግፍ ግድያ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) እና ሰማያዊ ፓርቲ፤ የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብት ኮሚሽንና ሌሎችማውገዛቸው አግባብ አለው። ህወሓቶችማውገዝን እንደተራና እንደ ተለመደ ነገር ያዩታል። ስለዚህ፤ ወሳኙ አቋምና ሂደት፤ ግድያውን የፈጸሙት ግለሰቦች ለፍርድ እንዲቀርቡ ያልተቆጠበ ትግልና ድምጽ ከማሰማቱና አገዛዙን ከመለወጡ ላይ ነው። ሕዝቡ እምቢተኛነቱን እንዲቀጥል ከማስተጋባቱ ላይ ነው። ስርነቀል ለውጥ እንዲካሄድ ከመደጋገፉ ላይ ነው።

ህወሓትግድያውን የፈጸመው “ዘርፈ ብዙ ማሻሻዮችን አደርጋለሁ” ብሎ የኢትዮጵያንና የዓለምን ሕዝብ ለማሳመን መግለጫ ባወጣ በማግሥቱ ነው። ከዚህ በፊት ገዢው ቡድን የሚያወጣቸውን ማዘናጊያዎች ለይተን እንድናያቸው፤ እንዳንታለል የሚል ትንተና አቅርቤ ነበር።ማዘናጊያዎችን በተከታታይ ማውጣት የገዢዎቹ የተለመደ ራስን ያማቆየት ስልት ሆኗል። ታዲያ፤ ይህ “እየማለ” የሚገድል ገዢ ቡድን እንዴት ሊታመን ይችላል? ገዢው ቡድን ሊታመን የሚችልበት መስፈርት ፈልጌ ላገኝ አልቻልኩም። እንዲያውም የአፈናውና የጭካኔው ሁኔታ እየተባባሰ ቢሄድ አያስገርምም።

በቅርቡ ከህወሓት እጅ አምልጦ ለጥቂት ግለሰቦች የተላከ የምስጢር ሰነድ የማህበረሰባዊ ሜድያን እንዴት ለመቆጣጠር እንደሚቻል ጥናትና ምክር ያቀርባል።የፖለቲካ ንግድና የበላይነት የሚካሄድባቸውን ቁልፍ ዘርፎች የሚጠቁመው ሰነድ የገመገማቸውን አራት አስኳል ስልቶች በአጭሩ ላቅርባቸው።

  1. በእድገት መጠን ላይ የሚደረገው ንግድ

ህወሓት እድገትንና ልማትን በራሱ ቋንቋ ገልብጦ የተለየ ትርጉም እንደሰጣቸው ጥናቶችና ትንተናዎች ያሳያሉ። ለምሳሌ፤ በቅርቡAxiosየተባለው የአሜሪካ ተቋም “The world’s fastest growing economy, is one of its poorest nations” በሚል ርእስ እንዲህ ብሏል። “The world’s fastest growing economy is not India (6.7% in 2017) or China (6.8%), but Ethiopia, according to a World Bank estimate that puts the East African country’s 2017 growth at 8.5% and projects 8.2% growth in 2018, ranking second only to Ghana (8.3%).”

ሰላምና እርጋታ በሌለባት ኢትዮጵያ “ፈጣን እድገት” ተከታታይ ሆኗል ሲባል ለህሊና ይቀፋል። እኔ ዓለም ባንክ የሚለውን የተሳሳተ የእድገት እርከን እንደማልጋራ በጥናቶቸ አሳይቻለሁ። ምክንያቱም፤ ዓለም ባንክ የገዢውን ፓርቲ ሰነዶችና መረጃዎች ተጠቅሞ የሚናገረውና የሚያስተጋባው እርከን፤ በመሬት ላይ ከሚታየው የእድገት ውጤት ጋር ግንኙነት የለውም። የኑሮውን ሁኔታ የሚያውቀው ተራው ኢትዮጱያዊ ስለሆነ፤ ከተራው ኢትዮጵያዊ ግብዓት የሚጠይቅ አካል የለም። ዓለም ባንክ የሚሰራውና የሚነጋገረው ከባለሥልጣናት ጋር እንጅ ከተራው ሕዝብ ጋር አይደለም፤ ሆኖም አያውቅም። አክሲዎስ የሚለውና እኔ የምከራከርባቸው ጉዳዮች ተመሳሳይነት አላቸው።

ታላቁን ስእል እንየው ይላል ድርጅቱ። “ With 102 million people, Ethiopia is the 2nd most populous country in Africa and the 12th most populous on earth. It’s also one of the world’s poorest countries —sitting just above Haiti and below Afghanistan in terms of GDP per capita — and its rapid growth has brought millions out of extreme poverty. But ethnic violence, a government crackdown and high unemployment are putting “one of Africa’s brightest success stories” at risk, per Eurasia Group’s Signal newsletter.” በመሬት ላይ የሚታየው ሃቅ የስራ እድል እንደሌለ፤ የኑሮ ውድነት፤ ጉቦ፤ ሙስና፤ የአስተዳደር ብልግናና ጭካኔ እንደቀጠለ። በልቶ ማደር ብርቅ እንደሆነ፤ ስደት እንደቀጠለ፤ አፈናው፤ ጭካኔውና ግድያው የተለመደ እንደሆነ፤ የዲሞክራሲ ጭላንጭል እንደሌለ ወዘተ ያሳያል።

እድገትና የእድገት ውጤት ከሰብአዊ መብት መከበር፤ ከነጻነት፤ ከፍትህ፤ ከሕዝብ ተሳትፎና ከዲሞክራሲ ጋር ቀጥተኛ የሆነ ግንኙነት አላቸው። ዓለም ባንክ ተሳስቷል የምልበትን ምክንያት The Economist, January 25, 2018 የባንኩን ከፍተኛ ኢኮኖሚስት ፓል ሮመርን በሚመለከት ያቀረበው ዘገባ ፍንጭ ይሰጠዋል። ልክ እንደማንኛውም በምእራብ መንግሥታት የበላይነት የሚመራ ድርጅት፤ ዓለም ባንክ ከፖለቲካ ዝንባሌ ውጭ አይሰራም ለማለት መረጃ የለንም። ለምሳሌ፤ ዓለም ባንክ የእያንዱን አገር የፖለቲካ ኢኮኖሚ አመራር ሁኔታዎች የሚያይበት መነጽር ከራሱና ከሚደጉሙት አገሮች የኢንቬስትመንትና የንግድ ጥቅሞች አንጻር መሆኑን ለማጤን ባንኩ ለደርግ መንግሥት ግዙፍ ብድር አይሰጥም ነበር፤ ለሰሜን ኮሪያና ለኩባ አያበድርም።የፖለቲካና የርእዮት ውሳኔ እንጅ ድህነትን ለማጥፋትና የአገርን የምርቶች ኃይል ለማዳበር የተደረገ ውሳኔ አይደለም።

በዓለም የታወቀው የዓለም ባንክ ዋና ኢኮኖሚስት ፖል ሮመር፤ የባንኩን ጥናትና ምርምር ክፍሎች በመተቸት፤ ድፍረት ያለው ወቀሳ ሰንዝሯል።“In an e-mail to several bank economists, sent last October and reported today in the Financial Times, Mr Romer was scathing about the bank’s “diagnostic” reports on individual countries and its broader intellectual culture.” ቀጥተኛ ትችቱ እንዲህ የሚል ነው። “I’ve never in my professional life encountered professional economists who say so many things that are easy to check and turn out not to be true…Imagine a field of science in which people publish research papers with data that are obviously fabricated. When someone points this out, the Internal Justice Bureau steps in [and] says that the concerns do not meet the burden of proof required for them to take action. Nothing happens.”እኔ የምለውን ወደ ጎን ትታችሁ እሱ የተቸውን ትኩረት ስጡት!!

ይህ አባባል ህወሓት ከሚፈበርከው የእድገትና የልማት እርከኖች ጋር ይዛመዳል። ስለሚዛመድ፤ ዓለም ባንክ ስለ ኢትዮጵያ አስደናቂ እድገት የሚሰጠን መረጃ የፈጠራ መረጃ ይሆናል ማለት ነው። ስለሆነም፤ ሃቀኝነት ያለው የእድገት መረጃ ለማግኘት አይቻልም። ፓል ሮመር የዓለም ባንክ ኢኮኖሚስቶች የሚያቀርቡት ዘገባና መረጃ የትንተና ሃቀኝነት “intellectual integrity” የለውም ማለት ነው።

ይህን ስል ትክክለኛ መረጃ ማግኘት ቀላል ነው ማለቴ አይደለም፤ አስቸጋሪ ነው። ኢኮኖሚስት እንደሚለው“The researcher’s findings may need to be replicable by another scientist. And they may need to show that their method was not reverse-engineered to produce a desired result. Research does not benefit from any presumption of methodological innocence. It has to prove its intellectual honesty and credibility.” የመረጃ ስህተት ወይንም ፖለቲካዊ የሆነ አድልዎ አለ ከተባለ ማን ያጣራዋል የሚል ጥያቄ ማቅረብ ይኖርብናል ማለት ነው።“When a researcher is accused of political bias or malpractice, the burden of proof falls not on the researcher but on the accuser. Reputations and livelihoods are at stake. There is a big difference between rejecting a proposition and repudiating a person…..Mr Romer clearly seems to believe that some of the bank’s economics is sloppy and intellectually dishonest. It cannot, in his view, meet anything like the heavy probative burden required of credible research.”

የኢትዮጵያን እድገት በሚመለከት ስመለከተው፤ የዓለም ባንክ የተዛባ መረጃ ጉዳቱ ለተጠቃሚው ድሃ የኢትዮጵያ ሕዝብ ጠበቃ አለመኖሩ ነው። አገር ቤት የሚኖሩ ምሁራንና ሳይንቲሶቶች በነጻነት ለመንቀሳቀስ፤ ጥናትና ምርምር ለማካሄድ አይችሉም። ማህበረሰባዊ ድርጅቶች እንዲፈርሱ ተደርጓል። ድንቁርና የሚረዳው ገዢውን ቡድን ነው።

የእድገቱ ውጤት ተማርኳል፤ ማራኪው የህወሓት ኃይል ስልጣኑን ለመቀጠል ቆርጦ ተነስቷል። ስልጣኑን ለማራዘም ተቃዋሚ ነው ብሎ የሚጠረጥረውን ሁሉ ማሳደድ፤ ማንበርከክ፤ ማፈን፤ ማሰር፤ መግደል፤ እንዲሰወር ማድረግ ስልቱ ሆኗል። የተቃዋሚው ክፍል መከፋፈል፤ በጥቃቅን ጉዳዮች ላይ ጊዜንና ኃብትን ማቃጠልና ማባከን ለአፋኙ አገዛዝ ግብዓት ሆኗል።

  1. በዲሞክራሲ ላይ የሚደረገው ንግድ

ህወሓት ጸረ-ዲሞክራሲ ነኝ ሊል አይችልም፤ የሚለው “የዲሞክራሲ ተቋም” ነኝ ነው። የራሳችን መስፈርቶች ብንጠቀም፤ እውነተኛ ዲሞክራሲ ማለት፤ የሕዝብ፤ በሕዝብና ለሕዝብ ተገዢ የሆነ የመንግሥት አገዛዝ ነው። ዲሞክራሲ አለ ከተባለ ሁለዘርፍ ችግሮች እየተፈቱ ሕዝቡ ፍላጎቱን የሚያሟላበት ሁኔታ ተፈጥሯል ማለት ነው። የስራ መስኮች እየተስፋፉና ምርት እየጨመረ፤ የነፍስ ወከፍ ገቢ እያደገ ይሄዳል ማለት ነው። እውነተኛ ዲሞክራሲ ለፍትሃዊና ለዘላቂ እድገት ወሳኝ ነው። ጭካኔና አፈና ግን የዲሞክራሲና የእድገት ጸር ወይንም ማነቆ ነው። ኢትዮጵያ ከሄይቲና ከአፍጋኒስታን ጋር እንጅ ከቦትስዋና ወይንም ከጋና ወይንም ከቬትናም ጋር ለመነጻጸር ያልቻለችበት መሰረታዊ ምክንያት አገዛዙና ፖሊሲው አፋኝ ስለሆኑ ነው። አፋኝ አገዛዝ የታፈነ ኢኮኖሚ ይፈጥራል፤ የገቢና የኑሮ ልዩነቶችን ያባብሳል ማለት ነው። ተደማምረው እርጋታን፤ ሰላምን፤ አብሮ መኖርን ይበክላሉ።

ሰነዱ እንዲህ ይላል። “የዲሞክራሲ አንዱ መገለጫ የሆነው ሀሳብን በነጻነት የመግለጽ እና የማስተላለፍ ጉዳይ ሰዎች ሀሳባቸውን እንዲገልጹተብሎ የሚተገበር ብቻ ሳይሆን ራሱ የልማት መሳሪያ ነው፡፡” ይህን ማለት ቀላል ነው። በገቢር ምን ይታያል የሚለው ነው ወሳኙ። “ይህን በተመለከተ የዲሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ ትግልእና አብዮታዊ ዲሞክራሲ የሚለው የድርጅታችን ሰነድ እንዲህ ይላል፡-

የሕዝቡን ሁኔታ፤ስሜቱንና ፍላጎቱን አስተሳሰቡን በእርግጠኛነት አውቆ ትክክለኛ ስልት ለመንደፍ በግብአትነትለመጠቀም የሚቻለው በስልቱ አፈጻጸም ሂደት የመጡ የአስተሳሰብ ለውጦችን በትክክለኛነት ተገንዝቦ ተፈላጊውንማስተካከያ ማድረግ የሚቻለው ህዝቡ በማንኛውም ጊዜ ሀሳቡን ሳይሸማቀቅ፤ በግልጽና በተሟላ ሁኔታ ማቅረብሲችል ነው፡፡ህዝቡ በማንኛውም ግዜ ሀሳቡን ሳይሸማቀቅ በግልጽና በተሟላ ሁኔታ መገልጽ የሚችለው ደግሞዲሞክራሲ ሲኖር ነው።” “ሕገመንግሥቱና አመራሩ” እንደዚህ ይላሉ የሚለው ብሂል በድርጊት ሲተረጎም ተጻራሪውን ያሳያል።ህጻናትን እየገደሉ “የመናገር ነጻነት” አለ ማለት ፍጹም ውሸት ነው። ይህን ነው የፖለቲካ ንግድ ጨዋታ የምለው።

“በማንኛውም ጊዜ ሃሳቡን ሳይሸማቀቅ ማቅረብ ይችላል” ከተባለ በሰላም ሃሳባቸውን የሚገልጹት የኦሮሞና የአማራ ወገኖቻችን ለምን ተገደሉ፤ ለምን ታሰሩ፤ ለምን እንዲሰወሩ ተደረጉ?ህወሓት/ኢህአዴግ የሚናገረው፤ የሚደሰኩረውና ለዓለም የሚያቀርበው የመብቶች መከበር ከሚሰራው ጋር ምንም ግንኙነት የላቸውም። ቢኖራቸው፤ ሕዝብ አይጨፈጨፍም ነበር፤ ሁሉም የፖለቲካ እስረኞች ይፈቱ ነበር።በህወሓቷ ኢትዮጵዩያ “ሃሳብን ሳይሸማቀቁ” መግለጽ ወንጀል ሆኗል።

በአጭሩ፤ ሕዝብ በነጻነት ድምጹን ሲያሰማ በተከታታይ የተከሰተው ውጤት ጭካኔና ግድያ ነው። ሰነዱን ቀረብ ብየ ስመለከተው ችግሩ አይኑን አፍጥጦ ይታያል። “ህወሓት/ኢህአዴግ ዲሞክራሲ ለልማት ያለው ፋይዳ ከፍተኛ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ ዲሞክራሲን በመጠቀም ጉዳት ለማድረስየሚፈልጉ አካላትን በተመለከተ ያለው አማራጭ አንድም ጉዳት ማድረስ የሚፈልጉ አካላት ሀሳባቸውን እንዳይገልጹማድረግ አልያም ሀሳባቸውን እንዲገልጹና ሀሳባቸው አንዲሸነፍ ማድረግ ነው” ይላል። ሃሳቦች ከሃሳቦች ጋር ተወዳድረው ሕዝብ የራሱን ውሳኔ ያድርግ የሚል አማራጭ አልቀረበም። የቀረቡት የህወሓት አማራጮች እንዲህ የሚሉት ናቸው።

  1. “የሶሻል ሚዲያ አርበኞችን ማንነት ማጋለጥ

“በሶሻል ሚዲያ በመጠቀም የህዝቡን ሰላማዊ ኑሮ፤ የስርዓቱን ህልውና ለመፈታተን የሚሞክሩ ግለሰቦች አብዛኞቹበውጪ ሀገራት በመሆን የሚሰሩ ሲሆን በሀገር ውስጥ የነሱን ተልዕኮ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ የሚተገብሩምአሉ፡፡የሶሻልሚዲያ አርበኞች የሚያስተላልፉቸው እያንዳንዱን መልዕክቶች ካላቸው ፓለቲካዊ፤ ኢኮኖሚያዊ፤ ማህበራዊእና ህገ-መንግስታዊ ስርዓት ላይ ከሚያስከትለው እንድምታ አንጻር በመተንተን አጸፋዊ ምላሽ ሊሰጥ ይገባል፡፡” ሕዝቡን ያፈነውና የሚያሰቃየው ቡድን ውጭ ያለውንም ለህዝብ መብቶች የሚታገለውን ተቆርቋሪ ኢትዮጵያዊ ለማፈን ዘመቻ እያካሄደ መሆኑ ነው።

ይህን ብዙ የታሰበበትን እርምጃ ለመውሰድ በሚል ስሌት፤ ህወሓት በመመሪያው ላይ እንዲህ የሚል ድምዳሜ አቅርቧል። “የሚሰጠው ምላሽ ስሜታዊነት የሚንጸባርቀበት ወይም የድርጅቱን መስመር የማይስት እንዲሆን በማዕከል ደረጃ ይህንስራ የሚያከናውን አሰራር መዘርጋት ይኖርበታል፡፡

  • በጥቅሉ ሲታይ በሶሻል ሚዲያ በመጠቀም ችግሮች ለመፍጠር የሚታትሩ ሃይሎች በሁለት ተከፍለው ሊታዩ የሚችሉሲሆን አንደኛው የጠባቡ ሃይል ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የትምክህት ሃይል ነው፡፡ እነዚህን ሃይሎች በዘርፋቸውበማስቀመጥ በእያንዳንዱ ሃይል ስር የተሰለፉትን ግለሰቦች እንዳላቸው የተከታይ ብዛት፤ የመልዕክታቸው አፍራሽነት ደረጃ በመለየት እጅግ አጥፊ ከሆኑት በመነሳት እስከ ዘገምተኛው ሃይል ያለውን መለየት ይገባል፡፡ይህንንም መነሻበማድረግ ግለሰቦች የሚያሰራጩዋቸውን መልዕክቶች ከስር ከስር በመከታተል የማጋለጥ ስር ሊከናወን ይገባል፡፡
  • በተጨማሪነት ግለሰቦች በግለሰብ ደረጃ የሚያሰዩዋቸው ባህሪያቶች የራሳቸው ቤተሰባዊ፤ ማህበረሰባዊ መነሻሊኖራቸው የሚችል በመሆኑ እነዚህነ ጉዳዮች በጥልቀት በማጥናት ግለሰቦች ፍሪዚ ሊያደርጉ የሚችሉበትን ስራዎችማከናወን ተገቢ ይሆናል፡፡”

በአገር ቤት ተቃዋሚ የሆኑ ግለሰቦችንና ስብስቦችን ማፈን፤ ማሳደድ፤ መግደልና ማሰር እንዲጠናከሩ እያደረገ፤ በውጭ ያለውን ተቃዋሚ “ጠባብና ትምክህተኛ” ኃሎች ናቸው ብሎ በመሰየም፤ “በአጥፊዎቹ ላይ” የተለየ ትኩረትና ክትትል እንዲደረግ ወስኗል። “ጠባብና ትምክህተኛ” ተብለው የተበየነባቸውን ክፍሎች ለመለየት አስቸጋሪ አይደለም።ቁም ነገሩ ግን፤ እነዚህ የውጭ ተቃዋሚ ኃይሎች የሚጠቀሙባቸው የሜድያ መሳሪያዎች ፌስቡክ፤ ትዊተር፤ ሊንድኪንና ተመሳሳዮቹ ከፍተኛ ክትትል እየተደረገባቸው መሆኑ ነው። ለዚህ አዲስ የተቀነባበረ ዘመቻ የሚያዋጣው፤ ከብሄር፤ ከግል ጥቅም፤ ከጉራ፤ ከቡድንና ከሌላ መለያ ባሻገር እየተረባረቡ፤ በአንድነትና በኢትዮጵያዊነት ዙሪያ እየተሰበሰቡና እየተደጋገፉገዢውን ፓርቲና በዲያስፖራው ዓለም ውስጥ በሰላይነትና በአጥፊነት የተሰማሩትን ተባባሪዎች ማጋለጥና በሕግ እንዲጠየቁ ማድረግ ይሆናል። የህወሕትን የጭካኔ ግድያዎች በአንድ ላይ ወደ ፍርድ ቤት የምናቀርብበት ወቅት አሁን ነው።

  1. “በሕገመንግሥቱ” የሚደረገው ንግድ

የማንኛውም መንግሥት የመጀመሪያ ስራው የዜጎችን ምኞት፤ ተስፋና ፍላጎት ለማሟላት መሞከር ነው። ምን አይነት መንግሥት ያስፈልጋል የሚለው ጥያቄ መመለስ ያለበት በጥናትና በሕዝብ ተሳትፎ እንጅ በጥቂቶች ስሌት ሊሆን አይችልም።  የህወሓት የውስጥ ጥናትና ድምዳሜ እንዲህ ይላል።

  • “የሀገራችን ህገ መንግስት በአንድ በኩል ሀገራችን የነበረችበትን መሰረታዊ ችግር የማንነት እውቅና ያለማግኘት መሆኑንበጽኑ በማመን፤ በሌላ በኩል ይህን ችግር ለመፍታት የማንነት መገለጫዎች ህገ-መንግስታዊ ዕወቅና እንዲያገኙ ያደረገበሌሎች ሀገራት የማይገኙ ተራማጅ የሆኑ ድንጋጌዎችን የያዘ ህገ-መንግስት ነው፡፡ህገ-መንግስት የግለሰቦችና የቡድንመብቶችና በእኩልነት እና ሳይነጣጥል መተግበር አለባቸው የሚል እና ይህንንም ለመተግበር የሚያስችሉዲሞክራሲያው የመንግስት አወቃቀር የያዘ ነው፡፡
  • ሕገ መንግስቱ ይህን ያህል ጠቀሜታ ያለው ሰነድ ቢሆንም ይህን ሰነድ በእያንዳንዱ የማህበረሰብ ክፍል ማስረጽ ላይየተሰራው ስራ ከህገመንግስቱ ዋጋ አንጻር ሲታይ እዚህ ግባ የሚባል አይደለም፡፡አሁንም ቢሆን በህገ-መንግስቱ ላይየተቀመጡት ድንጋጌዎች፤ ከድንጋጌዎች ጀርባ ያሉ የህዝብ ትግል የፈጠራቸው አስተሳሰቦች ይዘት እና ጥልቀት ላይ በቂየሆነ ግንዛቤ ሊሰጥ የሚችል ሃይል መፍጠር አልተቻለም፤ ግንዛቤው ያለውም ሃይል ይህን እንዲያስተላልፍ በቂ መድረክአልተዘጋጀለትም፡፡
  • እንዲያውም ባንዳንድ ቦታዎች ሕገ-መንግስት አከራካሪ ሰነድ መሆኑን ማሳየት እና ከዛ ውስጥህገ-መንግስቱን ያለመቀበል አዝማሚያን የሚያመለክት ሀሳብ እንዲንሸራሸር የሚደረግበት ሁኔታ ይታያል፡፡”

ችግሩ የአፈጻጸም ብቻ አይደለም። በብሄር/ቋንቋ የማይታረቁ ልዩነቶች ላይ የተመሰረተ “ክልላዊ ስርዓት” ስለሆነ ሊፈቱ የማይችሉ ሁኔታዎችን አስከትሏል። ሰው ሰራሽ ችግር የአስተሳሰብ ለውጥን ይጠይቃል።

ችግሩ ፌደራል መሆኑ አይደለም፤ የማንነት ጥያቄም አይደለም። ችግሩ ኢትዮጵያና የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚስፈልጋቸው ምን አይነት መንግሥትና የፌደራል ስርዓት ይሆን? የሚለው በአግባቡ ያልተወሰነ፤ ሕዝቡ ያልተወያየበትና በባለቤትነት ያልተጋራው መሆኑ ነው። የህወሓት/ኢህአዴግ አገዛዝ ከላይ የተጫነ እንጅ በሕዝብ ፈቃደኛነት የተመሰረተ አይደለም።

ስለዚህ፤ ችግሩን የፈጠረው ገዢው ፓርቲ ችግር መኖሩን ቢያምንና ቢቀበልም፤ መፍትሄውን የማቅረብ ብቃት፤ ጥራትና ችሎታ የለውም። ውሳኔ መስጠት ያለበት የኢትዮጵያ ሕዝብ እንጅ ጥቂት የጠባብ ብሄርተኞች ምሁራንና ልሂቃን ሊሆኑ አይችሉም። “በሌሎች አገሮች ያልተደረጉ ተራማጅ ድንጋጌዎች” የሚለው ብሂል ሌላ ማዘናጊያ ነው እንጅ የአሁኑ የጎሳ ፌደራል አገዛዝ ለአኟኩ፤ ለኦሞ ሽለቆውና ለሌላው ጭቁን ሕዝብ ምን ጥቅም አምጥቶለታል? በሕዝብ ስም የፖለቲካ ንግድ እየተካሄደ ነው የምለው ለዚህ ነው። ሌሎች የአፍሪካ መንግሥታት የናቁትን ህወሓት ለስልጣኑና ለጥቅሙ ሲል ያመልክበታል!

“የክልል” ነጻነትናየራስን ክልል የማስተዳደር መብት አለ የሚባለው ከእውነቱ የራቀ ነው። ለምሳሌ፤ የአማራውን ክልል በበላይነት የሚመራው የአማራው ህወሓት የመረጣቸውና እንዲወክሉት ስልጣን የሰጣቸው እንጅ የራሱ ተቆርቋሪዎች አይደሉም። የሚያዙትና የሚያስተዳድሩት ህወሓትና ህወሓት የፈለፈላቸው የአማራ ብሄር አባላት ናቸው። ይህ ባይሆን ኖሮ፤ የአማራው ፖሊስ ወይንም ሚሊሽያ የራሱን ወገኖች፤ በወልድያም ሆነ በወልቃይት፤ በባህር ዳር ሆነ በጎንደር አይጨፈጭፍም ነበር። የፈረሰውና መተካት ያለበት የኢትዮጵያ የመከላከያ ኃይል የሚያኮራ ታሪክ አለው። ሕጻናትና ሴቶችን አይገድል፤ አይጨፈጭፍም።

የአሁኑ “የመከላካያ ኃይል” የበላይ አዛዡና አስተዳዳሪው ህወሓትና የፈጠራችው ግለሰቦች መሆኑ አያከራክርም። ይህ ኃይል የህወሓት መሳሪያ ነው። በዚህ ምክንያት ነው፤ የአማራው ሕዝብ በአዴንን እስከሚሰለቸው ድረስ የተቸውና አንተ ልትወክለን አትችልም ያለው።

ለማጠቃለል፤ ታሪክ ያላትን ኢትዮጵያን ለመታደግ የምንችለው በአገራችን ዘላቂ ጥቅም ላይ የማያወላዳ አቋም ወስደን፤ ኢትዮጵያዊነት የዜግነት መለያችን ነው የሚል መርሆን ተቀብለን፤ በአንድነት፤ ለአንድ አገር ግዛታዊ አንድነትና ሉዐላዊነት፤ ለአንድና ለተሳሰረ ሕዝብ ደህንነት፤ መብትና የኑሮ መሻሻል ተደጋግፈን ለመስራት ስንወስን ነው።

የኢትዮጵያ ሕዝብ የፖለቲካ ሥልጣኑ ባለቤት ከሆነ ህይወቱንና ኑሮውን ለማሻሻል የሚችልበት የተፈጥሮ ኃብቱ ግዙፍ ነው። መስረታዊ ፍላጎቱን– በቂ ምግብ፤ ትምህርት፤ የጤና አገልግሎት፤ ዘመናዊ መጸዳጃ፤ ንጹህ ውሃ፤ መጠለያ ወዘተ– ለማሟላት የሚችል ሕዝብ ነው። አንድ አገር፤ አንድ ሕዝብ ስል ብርቃማ የሆኑትን የልዩ ልዩ ብሄረሰቦች እሴቶች ወደ ጎን እንተው ማለቴ አይደለም። እነዚህ እሴቶች ለኢትዮጵያዊያን ሁሉ የጋራ ጥሪቶች ናቸው፤ ከኢትዮጵያዊነት ጋር አይጋጩም።

ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!

January 30, 2018

Hiber radio Las Vegas ይህ ህብር ሬድዮ _የወቅታዊ መረጃ ምንጭ ነው። ህብር ሬድዮ በአቤኔዘር ኮሙኒኬሽን ሴንተር እየተዘጋጀ  ከላስ ቬጋስ ከተማ፣ ዘወትር ዕሁድ በአካባቢው ሰዓት አቆጣጠር ከምሽቱ 630 ሰዓት እስከሰዓት በህብር ሬዲዮ ድህረ ገጽ ወይም በቀጥታ በስልክ ለማዳመጥ  5639993994 ወይም 563999-3988 ወይም 712-432-8451 በመረጡት ቁጥር መደወል ብቻ በቂ ነው በእንግሊዝ ለምትኖሩ 01405770140 በስልክ ማዳመጥ ይቻላል። ዘወትር በድህረ ገጻችን፣ googel app store Hiber Radio ወደ ስልክዎ በመጫን ካልሆነም በዘሐበሻ እንዲሁም በተጠቀሱት ስልኮች ማዳመጥ ይቻላል።

 

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *