Hiber Radio: ሲያልቅ አያምርም፤ በሠፈሩትም መሠፈር አይቀርም !

US-election-2016-2

የአሜሪካ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ እየተጋጋለ ቁርጥ አለ ግምት ከሚሰጡት ስጋታቸውን የሚያነሱትን ጭምር እያስተናገደ ነው: ህብር ሬዲዮም በየጊዜወ የተለያዩ እንግዶችን በወቅቱ የአሜሪካ ምርጫ ላይ ማስተናገዱን አልፎ አልፎ ይቀጥላል: ከሬዲዮ ፕሮግራሙ ጎን ለጎን ከአሜሪካ ምርጫ ጋር የተገናኙ የተለያዩ መጣጥፎችን ለማስተናገድም እንሞክራለን።ሰሞኑን አሜሪካን ምርጫ በሩቁ ከሚያዩ አንድ ብዕረኛ የደረሰንን በድህረ ገጻችን ለንባብ ቅርበነዋል: የጸሐፊው ራሳቸውን ጉዱ ካሳ ብለዋል ሀሳብ የግላቸው ነው።ለመወያያ ይሆናልና ታነቡት ዘንድ እነሆ፤

ሲያልቅ አያምርም፤ በሠፈሩትም መሠፈር አይቀርም !

     ዳግማዊ ጉዱ ካሣ

“አንበሣን ፈርቼ ዛፍ ላይ ብወጣ ነብር ጠበቀኝ” የምንለው አሉን የምንላቸው ሁለትና (ከዚያም በላይ) አማራጮች እንከን ገጥሟቸው ስንጨነቅና ስንጠበብ ነው፡፡ የአሁን የኛ ሁኔታስ? በተለይ እኛ ኢትዮጵያውያን አማራጮቻችንን ሁሉ አንድ ባንድ እያጣን አይደለምን? ምን ቀረን? ኢትዮጵያን ወደንና ፈቅደን ለወያኔ አስረክበናል፡፡ መሸሻዎቻችን አሜሪካና አውሮፓም በኢኮኖሚ ድቀትና በአክራሪ ሙስሊሞች እየተንኮታኮቱ ናቸው – ሊለይላቸው አንድ እሁድ ቢቀራቸው ነው፡፡ ጥጋብን መቻል የሚያቅተው የዐረቡ ዓለምም በውስጥ ግጭቶች ከመበጣበጡም በተጨማሪ ብቸኛ የተፈጥሮ ሀብቱን – ነዳጁን – ሊጨርስ የቀረው ዘመን ጥቂት አሠርት ዓመታት ብቻ ናቸው፡፡ አፍሪካ፣ ላቲን አሜሪካና ካሪቢያን እንዲሁም ኤዥያም በየራሳቸው ችግሮች ተወጥረዋል፡፡ ሁሉም ጋ እሳት ነው – አንዱ ጋ የተዳፈነ ቢመስል በሌላው እየነደደ ነው፡፡ የምፅዓት ጊዜ በየደጃፋችን እያንኳኳ ያለ ይመስላል፡፡ የህልምና የእውን ሩጫችንን ቆም በማድረግ ይህንን ገሃድ እውነት እናስብ፡፡ እናስብናም ዞሮ መግቢያ የወል ሀገር እንድትኖረን መጎሻመጡን ትተን በጋራ እንንቀሳቀስ፡፡

“ኑሮ በአሜሪካ”ንን በተመለከተ አንጀት የሚበላ መጣጥፍ ከደቂቃዎች በፊት አነበብኩ፡፡ በዚያም እዚያ ስላሉ ወገኖቼ አዘንኩ፡፡ “ዱሮ”ን ተሸክሞ መኖር እንደማይቻልም ተገነዘብኩ፡፡ ዱሮ ዱሮ ነው፡፡ አሁንና ዱሮ ኅብረት የላቸውም፡፡ “የነበር ሲያወሩት ይመስላል ያልነበር፤ ያባብዬ ፎቶ እንዲህ ያምር ነበር” ብላለች አሉ አንዲት ልጅ በአባቷ የቀብር ሥነ ሥርዓት ላይ፣ የሙሾ ግጥሙን አስተካክዬ ባላስታውስ ይቅርታ፡፡ ለማንኛውም ብዙም ሳትደናገጡ ቀጣዮቹን አንቀጾች በጥሞና ተመልከቱ፤ ከዚያም ዓለም ወዴት እየነጎደች እንደሆነ ተረዱ፡፡ የአሜሪካና አውሮፓ ገነትነት በምን ፍጥነት ወደሲዖልነት እየተለወጠ እንደሆነም ተገንዘቡ፡፡ ማወቅ ቢጎዳም ካለማወቅ ግን ይሻላል፡፡

ስቲፍን ሌንድማን የተባለ አሜሪካዊ የፖለቲካ ተንታኝ የወቅቱን ፕሬዝደንታዊ የምረጡኝ ዘመቻ በሚመለከት ሰሞኑን ባስነበበን አስደንጋጭ ጽሑፉ የሚከተለውን ይላል፤

… ኦባማን ተክቶ ወደ ዋይትሃውስ የሚገባ ቀጣዩ የአሜሪካን ፕሬዝደንት የሚወርሰው ከ1929ዓ.ምቱ የመጀመሪያው የኢኮኖሚ ቀውስ ቀጥሎ በዚህ ዘመን የተከሰተውን ሁለተኛውን ታላቅ የኢኮኖሚ ቀውስ (second Great Depression) ነው፡፡ ይህ ቀውስ በአሥር ሚሊዮኖች የሚገመቱ ሥራ አጦች ወይም ዝቅተኛ ደሞዝ ተከፋዮች የሚበዙበትና በኢኮኖሚና በሥልጣኔ ዳብሯል ከሚባለው የአንደኛው ዓለም ዜግነት ወጥተው ወደሦስተኛው ዓለም ደረጃ እንዲወርዱ በልዩ ሥልት እየተገፉ ያሉ አሜሪካውያንን የያዘ ነው፡፡ ፕሬዝደንቱ የሚረከበው ችግር ቃላት ሊገልጹት ከሚቻላቸው በላይ እጅግ ውጥንቅጥና ውስብስብ ነው፡፡

ወደ ግማሽ አካባቢ የሚጠጋው የአሜሪካ ሕዝብ ድሃ ነው ወይም ወደ ድህነት ጫፍ እየተነዳ ነው፡፡ ብዙ ቤተሰቦች የዕለት እስትንፋሳቸውን ለማቆየት ከሁለት ቦታዎች በላይ መሥራት አለባቸው፡፡ ጥሩ ገቢ ያስገኛሉ የሚባሉ ብዙ ሥራዎች ከአሜሪካውያን ጉሮሮ እየተነጠቁ በርካሽ ደሞዝ ለሚቀጠሩ የውጭ ሀገራት ዜጎች እየተሰጡ ናቸው፡፡ ያሉት ሌሎች ሥራዎችም ቢሆኑ ደህና ደሞዝ የማያስገኙ፣ ጥቅማ ጥቅምም የሌላቸውና ጥቂት ሰዎች በጊዜያዊነት ወይም በትርፍ ሥራነት የሚቀጠሩባቸው ናቸው፡፡ የዜጎች ሕይወት አሳሳቢ ሁኔታ ውስጥ ይገኛል፡፡

ለአቅመ ሥራ ከደረሰው የአሜሪካ ሕዝብ መካከል ሩብ ያህሉ ሥራ ማግኘት አይችልም – ይህም የሆነው ሥራ ስለሌለ ወይም የሥራ ዕድል ስላልተመቻቸለት ነው፡፡ የአዳዲስ ሥራዎችን መፈጠር የሚዘግበው የሌበር ዲፓርትመንት የሚያወጣው ወርኃዊ ዘገባም የውሸት ነው፡፡ ሥራዎች ተከፈቱ ብሎ የሚያወራው መዝገብ ላይ እንጂ መሬት ላይ የሉም [ወይ የቦለቲካ መመሳሰል! የአሜሪካ መንግሥትም ወያኔ ሆነ ማለት ነው?] ሕዝብን የተሳሳተ መረጃ መቀለብ ሆን ብለው ተያይዘውታል፡፡[የአሜሪካን ሕዝብ በ2016 ኤፕሪል ላይ በተካሄደ የሕዝብ ቆጠራ 323, 730, 000 መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ ምንጭ – https://en.wikipedia.org/wiki/Demography_of_the_United_States]

የኦባማ መንግሥት ሥራን በመፍጠር ሣይሆን በተቃራኒው ሥራን በማጥፋት ይታወቃል፡፡ ስለሥራ መስክ ፈጠራና ስለማኅበራዊ ችግሮች ማስወገድ ዙሪያ አሁን ለዋይትሃውስ በመወዳደር ላይ የሚገኘው ትራምፕ ምንም ያለው ነገር አለመኖሩ ደግሞ ይገርማል፡፡…(በቅንፍ የተሰጡ አስተያየቶች/መረጃዎች የራሴ ናቸው)

 

አዎ፣ አሜሪካ ጣጣ ውስጥ ገብታለች፡፡ ዕዳዋ ራሱ 19.2 ትሪሊዮን ዶላር መሆኑ ራሱ ትልቅ ራስ ምታትና ከመሆኑም በተጨማሪ መቼ ተከፍሎ እንደሚያልቅ መገመትም አይቻልም – ይቺ ከመወለዷ እያረጀች የምትገኝ የዓለም ኃይል አገር ዐይን ገባት መሰል “ወፍራም ውሻ አለ ሲሉት ይሞታል” ዓይነት ሆናለች፡፡ ይህ የቀልድ የሚመስል የዕዳ ቁጥር እየጨመረ እንጂ ባለበት እንኳን ሊረጋ አለመቻሉ ደግሞ ብዙዎችን እያስደነቀ የሚገኝ አሳዛኝ ክስተት ነው፡፡

አሜሪካ የሁሉም ዜጋ ንብረት እንደመሆኗ ሁላችንም “አንቺ ቸኳላ አሜሪካን ሆይ ወዴት እየሄድሽ ነው? አንቺ ቀልቃላ የምንዱባን መጠጊያ አሜሪካ ሆይ ሩጫሽ ለምን ፈጠነ?” ብለን በጋራ እንጠይቃት፡፡ “ስንት በረንዳ አዳሪዎችን፣ ስንት ባለዕዳ ዜጎችን፣ ስንት አደንዛዥ ዕፅ አዘዋራችንና ተጠቃሚዎችን፣ ስንት ከባህልና ከሃይማኖት ያፈነገጡ ጉግማንጉጎችንና ፍናፍንቶችን፣ ስንት የአፍሪካውያን ሀብትና ንብረቶችን፣ ስንት ኢትዮጵያውያን የፖለቲካና ኢኮኖሚ ወንጀለኞችን፣ ስንት ነፍሰ ገዳዮችን… በጉያሽ ውስጥ ወሽቀሽ ይዘሻል? እስከመቼስ የወመኔዎች ዋሻ እንደሆንሽ ትቆያለሽ?” ብለንም እንጠይቃት፡፡ እንዲህ ብለን ደግሞ እናስጠንቅቃት፡- “አሁን ግን ጉድሽ!! አንዳንድ ቅን መሥራች አባቶችሽ ካቀዱት መንገድ ውጪ የሚጓዙ ፒራሚዳውያኑ አሰለጥ ልጆችሽ ሞትሽን እያፋጠኑና አምነው የተጠጉ ሌሎች የዓለም ዜጎችንም መድረሻ እያሳጡ ይገኛሉ፤ ስላንቺ የተነገረውም ትንቢት ሙሉ በሙሉ ሊፈጸም የቀረው ጊዜ በጣም አጭር ይመስላል፡፡ ስለዚህ ባፋጣኝ ንስሃ ካልገባሽና ወደ ቀናው መንገድ ካልተመለስሽ አንቺን አያድርግ፡፡ አሣርሽ ይበዛልና፡፡”

 

አውሮፓስ?

 

የአውሮፓም ዕጣ ፋንታ ከአሜሪካው የተለዬ አይደለም፤ እዚያም ቤት ነገር አለ፡፡ በዚያ በኩልም የሚያስደስት ነገር የለም – መልካም ዜና ዱሮ ቀረ፡፡ አይሲስ የሚባለው አሜሪካን ሠራሹ አሸባሪ ቡድን ከመካከለኛው ምሥራቅ በገፍ የሚያባርራቸው በጭካኔና በኋላ ቀርነት ከርሱ ብዙም የማይተናነሱ ዜጎች አውሮፓን እያጥለቀለቁ ናቸው፡፡ የአውሮፓ ድንበሮች ወትሮም ልል በመሆናቸው ማንም እየገባ በአሁኑ ወቅት አውሮፓውያኑ ራሳቸው በስቃይና በመከራ እንዲኖሩ ተገደዋል፡፡ የሚገቡባቸው ስደተኞች በሃይማኖትና በሥልጣኔ ደረጃ ከአውሮፓውያኑ በእጅጉ ስለሚለዩና ኋላ ቀርም ስለሆኑ ፈረንጆቹ ተራ ዜጎች የሚያደርጉትን አጥተው ግራ ተጋብተዋል፡፡ ከእሥር የተፈቱ ያህል የሚቆጠሩት ስደተኞች ዕድሜ ልካቸውን ባገራቸው ታፍነው ስለከረሙ በተለይ አውሮፓውኑን ሴቶችና ሕጻናነት አስገድደው በመድፈርና የተለያዬ አካላዊና ሥነ ልቦናዊ አደጋ በማድረስ የተረጋጋና ሰውኛ ሕይወት ይኖር የነበረውን አውሮፓዊ እንደጭራቅ እያሸበሩት ይገኛሉ፤ ነፃነትን የማያውቅ ሰው ነፃነትን ሲያገኝ አጠቃቀሙን አያውቅበትምና እነዚህ መጤዎች በሰው ሀገር ውስጥ ባለቤቶቹን መቆሚያ መቀመጫ እያሳጡ አስመርረዋቸዋል፡፡ መንግሥታቱም በዚህ በፈረደበት ሰብኣዊ መብት ጥበቃ ተብዬና እንግዳን ማክበር በሚለው ፈሊጥ እየተዘናጉ የገዛ ዜጎቻቸውን ለጭራቆች አጋልጠው ይልቁንም ይባስ ብለው ለወንጀለኛ ስደተኞች ከለላና ጥበቃ እያደረጉ ናቸው – ዕንቆቅልሽ ነው፡፡ ስለዚህም ነዋሪው ዜጋ የሚደርስበትን ነገር በማመንና ባለማመን መካከል ፈዝዞና ደንግዞ “የፈጣ ያለህ” እያለ ይገኛል – ሊያውም ከፈጣ ጋር ያልተቆራረጠው ጥቂቱ ዜጋ፤ ሌላውማ ነገር ዓለሙን እርግፍ አድርጎ ትቶ የራሱን ሥልጣኔ አምላኪ ሆኗል፡፡ ከጥቃት የማይከላከልልህ መንግሥት አይግጠምህ – ኢትዮጵያውያንም የገጠመን ችግር አንደኛው ይህን መሰሉ ነው፡፡ ለምሣሌ ጋምቤላ ውስጥ ያ ሁሉ ሕዝብ ሲያልቅና ሰውን ያህል ትልቅ ሀገራዊ ሀብት ተዘርፎ እንዲለቀቅ በገንዘብ ለድርድር ሲቀርብ መንግሥት ቢኖረን ኖሮ ስንትና ስንት የመልሶ ማጥቃትና የበቀል እርምጃ በተወሰደ ነበር፡፡ አልታደልንም፡፡

አውሮፓን እያሰጋት ያለው በዋናነት እስላማዊ አክራሪነት ነው፡፡ እንደሚታወቀው የአውሮፓ ሕዝብ ቁጥሩ ከጊዜ ወደጊዜ እየቀነሰ መጥቶ አሁን አሁን እንዲያውም – የተለዬ እርምጃ ተወስዶ ችግሩ እየተሻሻለ ካልመጣ በስተቀር – በሚቀጥሉት ሃምሣና ስልሣ ዓመታት ውስጥ የሕዝብ ቁጥራቸው ወደ ዜሮ የሚወርድባቸው ሀገራት ሊኖሩ እንደሚችሉ እየተነገረ ነው፡፡ በዕንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንደሚባለው በዚህ መሠረታዊ ችግራቸው ላይ ከፍ ሲል ለመግለጽ እንደተሞከረው በሃይማኖትም በባህልም በሥነ ልቦናም በአስተሳሰብና አመለካከትም በሌላውም ሁሉ በፍጹም የማይገናኙ በአብዛኛው ባላገር የሆኑ ስደተኞች ሲያጥለቀልቋቸው እነዚህ የአውሮፓ ሰዎች እንኳንስ ሰው ሊፈጥሩ የራሳቸውን መፈጠር ራሱ ሊጠሉና ሊረግሙ ይችላሉ፡፡ ስለሆነም አውሮፓ ቀስ በቀስ የአይሲስ ግዛት ልትሆን የምትችልበት አሣዛኝ አጋጣሚ ሊፈጠር ይችላል፡፡ አይሲሶች ራሳቸው እንደሚሉት ሮም ከተማን የካሊፌቱ ዋና መቀመጫና መናገሻቸው አድርገው አውሮፓንና መላውን ዓለም በሸሪዓ ለማስተዳደር ትልቅ ዕቅድ አላቸው፡፡ አይሆንም ደግሞ አይባልም፡፡ ሰባራ ክላሽን የያዙ ሰባት ንፍጣቸውን ያልጠረጉ ሕጻናት ወያኔዎች ለ17 ዓመታት ታግለውና ከተባበራቸው ኃይል ጋር ተባብረው ኢትዮጵያን የመሰለች ትልቅ ታሪካዊት ሀገር እንዲህ ማዋረድና ማበለሻሸት ከቻሉ አይሲስን የመሰለ ዐረመኔና ጨካኝ ሰይጣናዊ ፍጡር ዓለምን አይቆጣጠርም ብሎ ማሰብ የዋህነት ነው፡፡ የሚፈልጉትን ግብ ለመምታት ፍቅርና ውዴታ አላዋጣ ካለ እንደ ጭካኔ የሚያዋጣ ትልቅ ግብኣት የለም፡፡ የጭካኔ ተግባር መጨረሻው አያምርም እንጂ የፈለግኸውን ግብ መምታት ያስችልሃል፡፡ “ደፋርና ጭስ” የምንለውም እኮ ለዚህ ነው፡፡ እንጂ ከስድስት ሚሊዮን ሕዝብ አብራክ የወጡ ቆራጥ ጮሌዎች በምን ሒሣብ ነው 90 ሚሊዮን ሕዝብ ሊያሸኑ የሚቻላቸው? አስቡት፤ የፈለገ የውጪ ኃይል በምክርም ይሁን በመረጃና በሎጂስቲክስ ቢያግዛቸው እኛ ወንዶች ብንሆን (ሴቶችም ጭምር ብንሆን of course) ዝምባችንን እሽ ማለት ይቻላቸው ነበርን? እንዴት ተደርጎ! እነዚህ እርጉም ወያኔዎች ወንዝ ቀርቶ የደረቀ ቦይ የማያሻግር ያን የመሰለ ቆሻሻ ዓላማ ይዘው እዚህ የደረሱት በተንኮላቸውና በዐረመኔያዊ ተግባራቸው መሆኑን እንግዲህ ልብ ይሏል፡፡ ደህና ዓላማ ቢኖርህም አንዳንዴ ጨከን ካላልክ ጉድ ትሆናለህ ወንድሜ፤

ትመር እንደሆነ ምረር እንደኮሶ

አልመር ብሎ ነው የተበላው ዱባ (ኤዲያ!ግጥሙ ጠፋኝ እባክህ) የሚባለውስ ለዚህም አይደል?

የጸሐፊው ኢሜይል ma74085@gmail.com

ህብር ሬድዮን በህብር ሬዲዮ ድህረ ገጽ ወይም በቀጥታ በስልክ ለማዳመጥ 712 -432-8451 መደወል ብቻ በቂ ነው በእንግሊዝ ለምትኖሩ በ01405770140 በስልክ ማዳመጥ ይቻላል። ዘወትር በድህረ ገጻችን፣ ከ googel app store Hiber Radio ወደ ስልክዎ በመጫን ካልሆነም በዘሐበሻ እንዲሁም በተጠቀሱት ስልኮች ማዳመጥ ይቻላል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *