Hiber Radio: በኢትዮጵያ የትግራይ የበላይ ተጠቃሚነት ግልፅና ተጨባጭ ማስረጃ

ከአማራና ኦሮሞ ትብብር ይለምልም ፕሮጀክት (አኦትይፕ)

ከዚህ በታች የቀረበው ሰንጠረዥ ከኢትዮጵያ የማዕከላዊ ስታትስቲክስ ኤጀንሲ የተገኘ መረጃ ሲሆን። ይህ መረጃ እኤአ በ2014 በኤሮፓን ጆርናል ኦፍ ቢዝነስ ኤንድ ማኔጅመንት በሆነ ጆርናል ላይ ከታተመ የምርምር ፅሁፍ የተገኛ ነው። ይህ መረጃ በኢትዮጵያ መንግስት በይፋ የወጣና በአለም አቀፍ ተቋማትም የተረጋገጠ ነው። ይህ መረጃ ወያኔዎች በግልፅ ያመኑት ሲሆን ሌላ የሚደበቁትና የሚያጭበረብሩት ብዙ መረጃ እንዳለ ደግሞ ግምት ውስጥ መግባት ይገባዋል።  ወያኔዎች ባመኑት መረጃ ይህን የሚያህል ለትግራይ አድሎና የትግራይ የበላይነት ካለ በተደበቁት መረጃዎች ውስጥ የእጥፍ እጥፍ አድሎና የበላይነት እንዳለ መገመት ቀላል አይደለም። መረጃው የሚያመለክተው ኢትዮጵያ ውስጥ እኤአ ከ1996 እስከ 2009 ድረስ በሰራ ሶስት ዓመታት ውስጥ ስለተመሰረቱት እንዱስትሪዎች የተመለከተ ነው። በዚህ መረጃ መሰረት በአገሪቱ ውስጥ በ2009 የተመዘገቡት ኢንደስትሪዎች 40 ፐርሰንቱ የሚገኙት በአዲስ አበባ፣ 9 ፐርሰንት በትግራይ ክልል፣ 10 ፐርሰንት በአማራ፣ 20 ፐርሰንት በኦሮሚያ፣ 13 ፐርሰንት በደቡብ፣ 0.6 ፐርሰንት በአፋር፣ 0.6 ፐርሰንት በሶማሌ፣ 0.1 ፐርሰንት በቤንሻንጎል፣ 0.1 ፐርሰንት በጋምቤላ፣ 1.2 ፐርሰንት በሐረር፣ 2 ፐርሰንት በድሬዳዋ ነው። ይህ መረጃ እንደሚያመለክተው የትግራይ ክልል ከአገሪቱ የሕዝብ መጠን 5 በመቶ በሚገመት የሚኖርበት ክልል የኢንዱስትሪ ባለቤት ድርሻው ግን 9 መቶ ይደርሳል ማለት ነው። ይህ ማለት የትግራይ ክልል መሆን ከሚገባው አንፃር በእጥፍ በሚጠጋ መቶ ፐርሰንት ሲበልጥ፤ በአንፃሩ ከአገሪቱ የሕዝብ መጠን ወደ 30 በመቶ በሚገመት የሚኖርበት የአማራ ክልል የኢንዱስትሪ ድርሻው 10 በመቶኛ ሲሆን ይህም መሆን ከሚገባው አንፃር በሁለት እጥፍ ማለትም በሁለት መቶ ፐርሰንት ያነሰ ነው።

ከአገሪቱ የሕዝብ መጠን ወደ 34 በመቶ በሚገመት የሚኖርበት የኦሮሚያ ክልል የኢንዱስትሪ ድርሻው 20 በመቶኛ ሲሆን ይህም መሆን ከሚገባው አንፃር በሁለት ሦስተኛ እጅ ወይም 75 ፐርሰንት ያነሰ ሲሆን። በደቡብ ክልልም ከአገሪቱ የሕዝብ መጠን ወደ 20 በመቶ በሚገመት የሚኖርበት ክልል የኢንዱስትሪው ድርሻው 13 በመቶ ሲሆን ይህም መሆን ከሚገባው አንፃር በግማሽ በላይ ወይም 53 ፐርሰንት ያነሰ ነው። በአፋር ክልልም ከአገሪቱ የሕዝብ መጠን ወደ 2 በመቶ በሚገመት የሚኖርበት ክልል የኢንዱስትሪው ድርሻው 0.6 በመቶኛ ሲሆን ይህም መሆን ከሚገባው አንፃር በሁለት እጥፍ ወይም 200 መቶ ፐርሰንት ያንሳል። በኢትይጵያ ሶማሌ ክልል ከአገሪቱ የሕዝብ መጠን ወደ 6 በመቶ በሚገመት የሚኖርበት ክልል የኢንዱስትሪው ድርሻው 0.6 በመቶኛ ሲሆን ይህም መሆን ከሚገባው አንፃር በአስር እጥፍ ያህል ያንሳል። በቤንሻንጉልም ከክልልም የኢንዱስትሪው ድርሻው 0.14 በመቶኛ ሲሆን ይህም ክልሉ ከሚገባው አንፃር በአስር እጥፍ ያህል ያንሳል። በጋምቤላ ከክልልም የኢንዱስትሪው ድርሻው 0.18 በመቶኛ ሲሆን ይህም ክልሉ ከሚገባው አንፃር በእጥፍ ያህል ያንሳል። በአዲስ አበባ ላይ የሚደረገው የኢንዱስትሪ ግንባታ ደግም እጅግ የበዛ በመሆኑ የአገሪቱ የኢንድስትሪ ልማት 40 በመቶ የሚሆነው በአዲስ አበባ ይገኛል። አዲስ አበባን ደግሞ በአብዛኛው የተቆጣጠሩት የኤፈርት፣ የአላሙዲን፣ ወያኔዎችና የወያኔዎቹ ሸሪኮች የሆኑ የውጭ ካምፓኒዎች እንደሆነ በሕዝቡ በሚገባ ይታወቃል። በአዲስ አበባ የሚደረገውን አጠቃላይ የኤንድስትሪ ግንባታ ህወሃት በበላይነት እንደሚቆጣጠረው ከማንም የተሰወረ አይደለም። ህወሃት ከትግራይ ውጭ ያለው ትልቁ ዋሻው አዲስ አበባ ነው።  ይህ እንግዲህ በግልፅ እንደሚያሳየው በክልሎች በተደረገው የኢንዱስትሪ ግንባታ በተመለከተ የትግራይ ክልል ብቻ ከሚገባው በላይ በእጥፍ የተጠቀመ ሲሆን ሌሎች ክልሎች ደግሞ የሚገባቸውን አለማግኘታቸው ብቻ ሳይሆን በብዙ እጥፍ ማግኘት የሚገባቸውን የተነፈጉበት ሁኔታ ነው። ይህ እንግዲህ የትግራይ ክልል የበለጠ ለገበያ አመቺ የሆነ፣ በጥሬ ዕቃ አቅርቦት ብልጫ ኖሮት ወይም ለትራንስፖርት የበለጠ አመቺ ሆኖ ቢሆን ብዙ ላይገርም ይችል ነበር። ነገር ግን በእነዚህ መስፈርቶች ሲታይ የትግራይ ክልል ከሌሎች ክልሎች በጣም የሚያንስ እንጂ የሚሻል አይደለም። ስለዚህ ይህ የህወሃት የጠባብ ቡድንነትና የአድሎአዊ አገዛዝ ውጤት ብቻ ነው። ይህ አገሪቷ ትተዳደርበታለች የሚባለውን የፌደራል ሥርዓት ሕግ ያፈረሰ፣ ሕገ መንግስቱን የጣሰና የሁሉም ህዝብ እኩል ተጠቃሚነትንና የአገራዊ አንድነትን ራዕይ የተፃረረ የህወሃት የፀረ ኢትዮጵያ ዓላማ ውጤት ነው።

ሌላው በጣም በጥሞና ሊታይ የሚገባው ነገር በየክልሉ ተገንብተዋል ስለሚባሉት ኢንደስትሪዎች የባለቤትነት፣ የአቅምና የጥራት ጉዳይ ነው። ከዚህ በታች የተቀመጠው ከከኢትዮጵያ የማዕከላዊ ስታትስቲክስ ኤጀንሲ በተገኘው መረጃ መሠረት በትግራይ፣ በአማራ፣ በኦሮምያ፤ በደቡብና በኢትዮጵያ ሱማሌ ክልሎች ስለተገነቡት ኢንዱስትሪዎች ንፅፅር ለማቅረብ ይሞከራል።

በመጀመሪያ በአማራ ክልልና በትግራይ ክልል የተገነቡትን ኢንደስትሪዎች ለማነፃፀር፤ ከዚህ በላይ የተቀመጠው ሰንጠረዥ እንደሚያመለክተው በአማራ ክልልና በትግራይ ክልል የተገነቡት ኢንዱስትሪዎች ያላቸው የብዛትም ሆነ የጥራት ልዩነቶች እጅግ የሚያስደነግጥ ነው። በመጀመሪያ ደረጃ የተገነቡት ኢንዱስትሪዎች ቁጥርና ድርሻ ከላይ እንደተገለፀው በትግራይ ክልል ከአገሪቱ የሕዝብ መጠን 5 በመቶ በሚገመት የሚኖርበት ክልል ኢትዮጵያ ውስጥ ከተገነቡት የኢንዱስትሪ ባለቤት ድርሻው ግን 9 መቶ ይደርሳል ማለት ነው ይህ ማለት የትግራይ ክልል መሆን ከሚገባው አንፃር በእጥፍ በሚጠጋ ሲበልጥ፤ በአንፃሩ ከአገሪቱ የሕዝብ መጠን ወደ 30 በመቶ በሚገመት የሚኖርበት የአማራ ክልል ኢትዮጵያ ውስጥ ከተገነቡት የኢንዱስትሪ ድርሻው 10 በመቶኛ ሲሆን ይህም መሆን ከሚገባው አንፃር በሁለት እጥፍ ያነሰ ነው። በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንደሚባለው እነዚህ በአማራ ክልል የተገነቡት ኢንዱስትሪዎች በትግራይ ክልል ከተገነቡት ጋር ሲነፃፀሩ በጣም ቀላልና አቅም የሌላቸው ኢንዱስትሪዎች ናቸው። ለምሳሌ ያህል በአማራ ክልል የሚገኙት 227 ኢንዱስትሪዎች የፈጠሩት የሥራ ዕድል 8005 ሲሆን፤ በትግራይ የተገነቡት 198 ኢንዱስትሪዎች ደግሞ የፈጠሩት የሥራ ዕድል 17 838 ነው። በአቨሬጅ ሲመነዘር በትግራይ ያለ አንድ ኢንደስትሪ በአማካኝ ዘጠና የሥራ ዕድል ሲፈጥር በአማራ ክልል ግን ሰላሳ አምስት ብቻ ይሆናል ማለት ነው። ይህ ማለት እንግዲህ ትግራይ የተገነቡት 198 ኢንደስትሪዎች አቅም አማራ ክልል ከተገነቡት 227 ኢንዱስትሪዎች በእጥፍ ይበልጣሉ ማለት ነው። በቀላል አገላለፅ የትግራይ አንድ ኢንደስትሪ ከሁለት የአማራ ኢንደስትሪዎች የበለጠ የሥራ ዕድል ፈጥረዋል ማለት ነው። በአጠቃላይ የምርት ዋጋም ሲታይ በትግራይ የተገነቡት 198 ኢንዱስትሪዎች ከአማራው ክልል 227 ኢንዱስትሪዎች በአማካኝ በሁለት እጥፍ ይበልጣሉ። ይህም ማለት በአማካኝ አንድ የትግራይ ኢንዱስትሪ አማራ ክልል ከሚገኝ ሶስት ኢንዱስትሪዎች የበለጠ የአጠቃላይ የምርት ዋጋ ይፈጥራል። በአትራፊነት ደረጃም ሲነፃፀሩ ለማወዳደር በሚያስደነግጥ ዓይነት የትግራይ ክልል የኢንዱስትሪ ሴክተር በሺህ በሚበልጥ እጥፍ ከአማራው ክልል የኢንዱስተሪ ሴክተር በትርፋነት ሲበልጥ። የአማራው ክልል የኢንዱስትሪ ልማት በኪሳራ የሚንገጫገጭና በጣም የደከመ የልማት ሴክተር ነው። የአማራው ክልል ኢንዱስትሪዎች በአብላጫው በኪሳራ የተዘፈቁ ቀላልና በጎጆ ኢንዱስትሪነት ሲመስሉ የትግራ ክልል ደግሞ እጅግ አትራፊ የሆኑ በመካከለኛና በከባድ ኢንዱስትሪዎች ይመሰላሉ። በቋሚ ንብረት ደረጃም በትግራይ የተገነቡት ኢንደስትሪዎች ከአማራው ክልል በአጠቃላይ አራት እጥፍ ይበልጣሉ።

ይህ እንግዲህ እንደሚያመለክተው በትግራይ ክልል በቁጥር ብቻ ሳይሆን ከሚገባው ድርሻ በላይ ኢንዱስትሪ የተገነባው፤ የኢንዱስትሪ ዓይነቶችና ጥራታቸውም ከአማራው ክልል እጅግ በሚገርም ሁኔታ ግዙፍ ናቸው። ይህ እንግዲህ አድሎ ብቻ ሳይሆን የግፍ ግፍ ነው። ይህንን በግልፅ እየተመለከቱ እንቅልፍ ተኝተው የሚያድሩ የብአዴን አመራሮችና አባላቶች እጅግ የሚገርሙ ናቸው። በጣም የሚገርመው ደግሞ በሰንጠረዡ ላይ እንደሚታየው በአድዋ የተገነቡት ሃያ ኢንደስትሪዎች ብቻ የፈጠሩት የሥራ ዕድል አማራ ክልል ከተገነቡት በሙሉ ኢንደስትሪዎች የበለጠ የሥራ ዕድል ፈጥረዋል። በአድዋ የተገነቡት ሃያ ኢንዱስትሪዎች 8687 የሥራ ዕድል ሲፈጥሩ በአማራ ክልል የተገነቡት 227 ኢንደስትሪዎች የፈጠሩት የሥራ ዕድል 8005 ነው። ይህ እንግዲህ የትግራይ የበላይ ተጠቃሚነት ብቻ ሳይሆን የብሔር አፓርታይድ ሥርዓት ነው። ሌላው አጠያያቂው ጉዳይ እነዚህ በአማራ ክልል ከተገነቡት ኢንዱስትሪዎች ምን ያህሉ ናቸው የክልሉ ነዋሪዎች የሆኑት፤ ምን ያህሉ ናቸው የህወሃትና የሸሪኮቻቸው የሆኑት። በቅርቡ በክልሉ በተነሳው ተቃውሞም ምን ያህሎቹ ናቸው የተቃውሞው ዒላማ የነበሩትና ለምን ብሎ በመጠየቅ ብዙ የኢንዱስትሪዎቹ ባለቤቶች የክልሉ ነዋሪዎች አለመሆናቸውንም ሊጠቁሙ ይችላል። ይህ እንግዲህ ሆን ተብሎ ክልሉን ለማድቀቅ በህወሃት ገዢ ዓላማ የተወጠነ ሤራ ነው።

በኦሮሚያ ክልልም ያለው ሁኔታ ከአማራው ክልል የባሰ የግፍ ግፍ እንጂ የተሻለ አይደለም። በመጀመሪያ ደረጃ የተገነቡት ኢንዱስትሪዎች ቁጥርና ድርሻ ከላይ እንደተገለፀው የትግራይ ክልል ከአገሪቱ የሕዝብ መጠን 5 በመቶ ሲገመት ኢትዮጵያ ውስጥ ከተገነቡት የኢንዱስትሪ ባለቤት ድርሻው ግን 9 መቶ ይደርሳል ማለት ነው ይህ ማለት የትግራይ ክልል ከሚገባው አንፃር በእጥፍ በሚጠጋ ሲበልጥ፤ በአንፃሩ ከአገሪቱ የሕዝብ መጠን ወደ 35 በመቶ በሚገመት የሚኖርበት የኦሮሚያ ክልል የኢንዱስትሪ ድርሻው 20 በመቶኛ ሲሆን ይህም መሆን ከሚገባው አንፃር በሁለት ሦስተኛ እጅ ያነሰ ነው። በተጨማሪም በኦሮሚያ የተገነቡት ኢንደስትሪዎች አርባ በመቶው የሚሆኑት በአዲስ አበባ በቅርብ ርቀት ባሉ አምስት ከተሞችው ውስጥ የተከማቹ ስለሆነ እነዚህ አብዛኛው ኢንደስትሪዎች የህወሃቶችና የሸሪኮቻቸው መሆናቸው በግልፅ የተረጋገጠ ሲሆን፤ በክልሉ በተናሳው ተቃውሞም ዒላማ እንደነበሩ ማንም የሚያውቀው ነው። ከትግራይ ከተገነቡት ኢንደስትሪዎችም ለማነፃፀርም ያህል ደምወዝና ክፍያን በተመለከተ በኦሮምያ ክልል ያሉት ኢንደስትሪዎች በአማካኝ ከትግራይ ክልል ካሉት ኢንዱስትሪዎች ለደምወዝ ክፍያ ከሚያወጡት በአምሳ በመቶ ያንሳሉ። ይህም ማለት በኦሮማያ ክልል ከትግራይ ክልል ይልቅ ጉልበት በርካሽ ይገኛል። በኦሮምያ ክልል የሚገኝ ሰራተኛ ከትግራይ ክልል ከሚገኘው ሰራተኛ ይበልጥ ይበዘበዛል። ይህ ማለት የኦሮምያ ክልል ነዎሪ ኢንዱስትሪውም የራሱ አይደለም፣ ለጉልበቱም ተመጣጣኝ ክፍያ አያገኝም። የግፍ ግፍ ማለት ደግሞ ይህ ነው።

በህወሃት መሪ እቅድ መሠረት የአማራ ክልል የሚቀማና የሚደቅ ክልል ሲሆን፤ የኦሮምያ ክልል ደግሞ የሚተራመስና የሚዘረፍ ክልል ነው። በዚህ ምክንያት የኦሮምያ ክልል የህወሃት ትልቁ የዘረፋ ኔት ወርክ በድርጅት፣ በቡድንና በግለሰብ ደረጃ የተዘረጋበት ክልል በመሆኑ በክልሉ የሚገኙት አብዛኛው ኢንዱስትሪዎች ከክልሉ ነዎሪዎች ጋር ያላቸው ቁርኝት እጅግ የላላ ነው። በዚህም ምክንያት ነው ለሕዝባዊ ተቃውሞ በቀላሉ ተጋላጭ የሆኑት። ለዚህም ሲባል በቅርቡ በኦሮምያ የሚኖሩ የህወሃቶች ማንነት እንዳይታወቅ ከመታወቂያ ደብተራቸው ላይ የትውልድ ቦታ ትግራይ የሚለው እንዲሰረዝ የተወሰነው። የክልሉ አመራሮችም ቢሆኑ እስከቅርብ ጊዜ ድረስ የህወሃት ጉዳይ አስፈፃሚ ሆነው ከማገልገል በስተቀር በክልሉ ስለሚገኙት ኢንዱስትሪዎች ምንም በቂ መረጃ የሌላቸውና በኢኮኖሚ የእኩል ተጠቃሚ ጥያቄዎችን ለማንሳት የማይችሉና የማይደፍሩ ሲሆን፤ የሚደረገው ኢፍታዊ ሁኔታ አስመርሯቸው ጥያቄ የሚያነሱ ግለሰቦችንም ሆኑ አመራሮችን በኦነግ፣ በአሸባሪነት በጠባብ፣ በሙሰኝነትና በብቃት ማነስ በማሳበብ በርካታዎች የተገደሉበት፣ የታሰሩበትና የተፈናቀሉበት ክልል ነው። የኦሮምያ ክልል አዛዥና ገዢ የበዛበት፤ የህወሃት ጀኔራሎች ያለገደብ የሚፈነጩበት፤ የኤፈርት፣ የሜተክና የአላሙዲን ኢንዱስትሪዎችና ኩባንያዎች በከፍተኛ ሁኔታ የሚመዘብሩት ክልል ነው። የኦሮሚያ ክልል በህወሃት የማፊያ ቡድኖች በከፍተኛና በአስከፊ ሆኔታ የተተበተብ ክልል ነው። የሕዝባዊ ተቃውሞውም ዋናው ዓላማ ይህንን የህወሃት የዘረፋና የማተራመሻ የማፊያ ኔት ወርክ ለመበጣጠስ ነው። ይህ የህወሃት የማፍያ ኔትወርክ ሊበጣጠስ የሚችለው በሕዝባዊ ትግል ሲሆን፣ ሕዝባዊ ትግሉም በአሸናፊነት እንዲጠናቀቅ ከአማራው፣ ከደቡቡና ከሌሎችም እኩልነትና ፍትህ ፈላጊ ፀረ ህወሃት የኢትዮጵያውያ ኃይሎች ጋር መተባበርና አብሮ መሥራት የግድ ይሆናል።

በደቡብ ክልልማ ያለው የኢንዱስትሪዎች ሁኔታ በብዛትም ሆነ በጥራት ከትግራይ ጋር ሲነፃፀር እጅግ የደከሙና ያነሱ ናቸው። በመጀመሪያ ከብዛት አንፃር ከላይ ለመግለፅ እንደተሞከረው ከአገሪቱ የሕዝብ መጠን ወደ 20 በመቶ በሚገመት የሚኖርበት ክልል የኢንዱስትሪው ድርሻው 13 በመቶ ሲሆን ይህም መሆን ከሚገባው አንፃር በግማሽ እጅ ያነሰ ነው። ነገር ግን የትግራይ ክልል ከአገሪቱ የሕዝብ መጠን 5 በመቶ ሲገመት ኢትዮጵያ ውስጥ ከተገነቡት የኢንዱስትሪ ባለቤት ድርሻው ግን 9 መቶ ይደርሳል ማለት ነው ይህ ማለት የትግራይ ክልል ከሚገባው አንፃር በብዛት በእጥፍ ይበልጣል። ለኃይለማርያም ደሳለኝ ሊደርስ የሚገባው መልእክት ይህ ደቡብ ከትግራይ በበእጥፍ የሚያንሰው ጉዳይ ሊሆን ይገባል። ብዛአነት፣ ሀብትና ብዛት ያለው ክልል እስከመቼ ድረስ አናሳ እየሆኑ መቀጠል ይገባዋል።

እነዚህ በደቡብ ክልል የተገነቡት ኢንዱስትሪዎች በትግራይ ክልል ከተገነቡት ጋር ሲነፃፀሩ በአብዛኛው የደከሙና ቀላል ኢንዱስትሪዎች ናቸው። ለምሳሌ ያህል በደቡብ ክልል የሚገኙት 282 ኢንዱስትሪዎች የፈጠሩት የሥራ ዕድል 7281 ሲሆን በትግራይ የተገነቡት 198 ኢንዱስትሪዎች ደግሞ የፈጠሩት የሥራ ዕድል 17 838 ነው። በአቨሬጅ ሲመነዘር በትግራይ ያለ አንድ ኢንደስትሪ በአማካኝ ዘጠና የሥራ ዕድል ሲፈጥር በደቡብ ክልል ግን ሃያ አምስት ብቻ ነው። ይህ ማለት እንግዲህ ትግራይ የተገነቡት ኢንደስትሪዎች አቅም ደቡብ ክልል ከተገነቡት ኢንዱስትሪዎች የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ በአራት እጥፍ በሚጠጋ ይበልጣሉ ማለት ነው። ይህ ማለት በአማካኝ በትግራይ የሚገኝ አንድ ኢንደስትሪ በደቡብ ካሉ አራት ኢንደስትሪዎች ይበልጣል ማለት ነው። በጣም የሚያስደነግጠው ደግሞ በአድዋ ብቻ የተገነቡት ሃያ ኢንዱስትሪዎች 8687 የሥራ ዕድል ሲፈጥሩ፤ በደቡብ ክልል የሚገኙት 282 ኢንዱስትሪዎች የፈጠሩት የሥራ ዕድል 7281 ነው። ይህ ማለት በትንሿ ትግራይ በሚገኝ አንድ ዞን ያለ የኢንዱስትሪ እንቅስቃሴ በህዝብ ብዛቱ የትግራይን ክልል በአራጥ እጥፍ በሚበልጠው ከደቡብ ክልል እጅግ የተሻለ ነው። በአጠቃላይ የምርት ዋጋም ሲታይ በትግራይ የተገነቡት 198 ኢንዱስትሪዎች ከደቡብ ክልል ከተገነቡት 282 ኢንዱስትሪዎች በአጠቃላይ የምርት ዋጋም በሶስት እጥፍ ወይም ሶስት መቶ ፐርሰንት ይበልጣሉ። ከትግራይ ጋር ሲነፃፀር በደቡብ ያሉት ኢንዱስትሪዎች እጅግ ደካማ ናቸው። በአትራፊነት ደረጃም ሲነፃፀሩ የትግራይ ክልል የኢንዱስትሪ ሴክተር በአምስት እጥፍ ወይም በአምስት መቶ ፐርሰንት ከደቡብ ክልል የኢንዱስተሪ ሴክተር ይበልጣል። በቋሚ ንብረት ደረጃም በትግራይ የተገነቡት 198 ኢንደስትሪዎች በደቡብ ክልል ከሚገኙት 282 ኢንዱስትሪዎች በአጠቃላይ በአምስት እጥፍ ይበልጣሉ። ይህ በጣም የሚያሳፍርና የሚያስደነግጥ ሁኔታ ነው። የኃይለማርያም ደሳለኝ ደቡብን እወክላለው ማለት እጅግ አሳፋሪ ነው። እንዲህ ያለ ፌዝና ንቀት በደቡብ ሕዝብ ላይ እየተፈፀመ የህወሃት ጉዳይ አስፈፃሚ ሆኖ መኖር ለደቡብ ኢትዮጵያ ህዝብ ብቻ ሳይሆን ለሁሉም ኢትዮጵያዊ የሚያሳፍር ነው። ይህን እያስፈፀመ በሰላም ተኝቶ የሚያድር ሰው በጣም ይገርማል።

በሌሎች በተቀሩት ክልሎች የሚታየው የኢንዱስትሪዎቹ ግንባታ የብዛት ሆነ የጥራት አድሎ በጣም የባሰ ነው። ለምሳሌ ከዚህ በታች የተቀመጠው ሰንጠረዥ እንደሚያመለክተው። የኢትዮጵያን ሱማሌ ክልል ብንወስድ፤ ክልሉ በህዝብ ቁጥሩ ከትግራይ የሚመሣሰል ቢሆንም በቆዳ ስፋት የትግራይን ሶስት እጥፍ የሆነ፤ አብዛኛ የክልሉ ነዋሪና ወጣት እስከ 80 ፐርሰንት በሚደርስ የሥራ አጥነት የሚሰቃይ፤ ክልሉ በከፍተኛ ድርቅ የሚጠቃ፤ በጣም የተዳከመ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ያለበትና በድህነት በጣም የደቀቀ ክልል ነው። ነገር ግን በፌደራል ሥረዓትና የብሔር ብሔረሰቦች እኩልነት ተከብሯል የሚል ሕገ መንግስት በፀደቀበት የህወሃት አገዛዝ ወቅት በአሰራ ሶስት አመታት ውስጥ በትግራይ ክልል 178 ኢንዱስትሪዎች ሲገነቡ በሱማሌ ክልል የተገነቡት 12 ብቻ ናቸው። የትግራይ ክልል በአስራ ሶስት ዓመታት ውስጥ የሱማሌ ክልል በ14 እጥፍ ወይም 1400 ፐርሰንት በብዛት የሚበልጥ የኢንዱስትሪ ግንባታ አድርጓል።

ከጥራትም አንፃር የሚታየው ልዩነት በጣም የሚያስደነግጥ ነው። በሱማሌ ክልል ያሉት ኢንዱስትሪዎች በአማካኝ የሥራ ዕድል የሚፈጥሩት ለ16 ሰው ሲሆን በትግራይ ያለው አማካኝ የሥራ ዕድል ለ90 ሰው ነው። ይህ እንግዲህ በትግራይ ያለ አንድ ኢንዱስትሪ በአማካኝ ከሱማሌ ካለ አንድ ኢንዱስትሪ በአማካኝ ስድስት እጥፍ ወይም በ600 ፐርሰንት የበለጠ የሥራ መፍጠር ብቃት አለው። በአጠቃላይ የምርት ዋጋ አማካኝም ሲታይ በትግራይ የተገነቡት ኢንዱስትሪዎች በአምስት እጥፍ ወይም በ500 ፐርሰንት ከሱማሌው ከተመሰረቱት በአማካኝ ይበልጣሉ። በአትራፊነት ደረጃም ሲነፃፀሩ የትግራይ ክልል የኢንዱስትሪ ሴክተር በአማካኝ በስድስት እጥፍ ከሱማሌ ክልል የኢንዱስተሪ ሴክተር ይበልጣል። በቋሚ ንብረት ደረጃም በትግራይ የተገነቡት ኢንደስትሪዎች በአማካኝ ከሱማሌ ክልል ከሚገኙት ኢንዱስትሪዎች በአማካኝ 23 እጥፍ ወይም 2300 ፐርሰንት ይበልጣሉ። በዚህ አንፃር በሱማሌ ክልል የተሰሩት ኢንዱስትሪዎች ከትግራይ ጋር በጥራታቸውና በብዛታቸ አንፃር ለማነፃፀር እጅግ የሚያሳዝን ነው። ይህም አልበቃ ብሎ በቅርብ ጊዜ የሱማሌ ክልል ለትግራይ ተፋናቃዮች በሚልዮኖች በሚቆጠር ግንዘብ እርዳታ አደረግ ሲባል ተሰምቷል፤ በከፍተኛ ድህነት ላይ የሚገኝ ግለሰብ ከእሱ ሺህ ጊዜ በላይ የሚበልጥ ላለው ግለሰብ እርዳታ እንዳደረገ የሚቆጠር የዘመኑ ምርጥ ቀልድ ሊሆን ይችላል።

ከላይ በሰፊው እንደተዘረዘረው በኢንዱስትሪው ዘርፍ የትግራይ ክልል ሌሎች ክልሎችን በብዛትና በጥራት የሚበለጠው እጅግ በገዘፈ ሁኔታ ነው። ቁጥሮችን ለመገመት በሚያስችል ዓይነት በሶስት እጥፍ ወይም ሶስት መቶ ፐርሰንት፣ አምስት እጥፍ ወይም አምስት መቶ ፐርሰንት፤ በስድስት እጥፍ ወይም ስድስት መቶ ፐርሰንት፤ በአንድ ሺህ ፐርሰንት፤ በሁለት ሺህ ፐርሰንት ወዘት ነው። ታዲያ ይሄ የትግራይ የበላይ ተጠቃሚነት ካልተባለ የትግራይ ዘራፊነትና ሌብነት መባል ይሻለዋል ወይ። የተቀረው የኢትዮጵያ ሕዝብ የጨዋነት ባህል ስላለው ክብር ባለው መንገድ የትግራይ የበላይ ተጠቃሚነት ማለቱ እንደ ወንጀል ስለተቆጠረ አሁን ግን የግፋ ብዛቱ ሞልቶ በመፍሰሱ አካፋና አካፋ ማለት ጀምሮ አስፈላጊውን እርምጃ ወደ መውሰድ ተሸጋግሯል።

ስለዚህ በኢትዮጵያ የትግራይ የበላይ ተጠቃሚነት የማያከራክርና በገሃድ የሚታይ ቁልጭ ያለ ሀቅ ነው። በአዲስ አበባና በሌሎች ትልልቅ ከተሞች የሚኖረው ኢትዮጵያዊ በየቀኑና በየሰዓቱ የሚጋፈጠው እውነታ ነው። በጣም የሚያሳፍር እውነታ፣ በዘር ማንነት ብቻ በአድሎ ከበርቴ መሆን። ሌላውን እያደኽዩና እየዘረፋ ባለሃብት መሆን፤ የአገሪቷን የወደፊት የእድገት አቅጣጫ በሚያጨናግፍ አይነት የአገሪቷን ቁልፍና በጣም አትራፊ የሆኑ ኢንደስትሪዎችን ከወያኔዎች ጋር ሽርክና ለሚገቡ የውጭ ካምፓኒዎች በመቸብቸብ ሀብታም መሆን፤ የአርሶ አደሩን መሬት በልማትና በኢንቬስትመንት ስም በመቀማት በመከፋፈልና ለሸሪኮቻቸው የውጭ ካምፓኒዎች በርካሽ በማከፋፈል ሀብታም መሆን። እነዚህን የመሳሰሉትን ከፍተኛ ወንጀሎች በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ የሚፈፀሙት ማንን ለመጥቀም ታስቦ እንደሆነ የኢትዮጵያ ህዝብ በግልፅ የሚያውቀውና እየተቃወመው የሚገኝ ጉዳይ ነው። የኢትዮጵያ ህዝብም በወያኔ እየተገደለ፣ እየታሰረና እየተሰቃየ የሚገኘው ይህንን ዓይነት አገርን የሚያጠፋ የወያኔ የዘረኝነትና የግፍ ሥርዓት በመቃወሙ ነው። አገር ቤት ሆኖ የትግራይ የበላይነት አለ በግልፅ በድፍረት መናገር የሚያሳስርና የሚያስገድል ነው። ነገር ግን ሁልም ኢትዮጵያዊ የሚያውቀው የአደባባይ ሚስጥር ነው። በተቀረው ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን እውነታ ህዝቡ በሚገባ የሚያውቀውና አጋጣሚምም ሲያገኝ በሚወሰደው እርምጃዎች ተቃውሞውን እየገለፀ ይገኛል። ነገር ግን እጅግ እንቅልፍ የሚነሳው ጉዳይ የወያኔዎች በግፍ ባለሀብት መሆን ብቻ ሳይሆን ዋናውና ትልቁና አሳሳቢው ጉዳይ ትግራይን ለማልማት የተቀረውን ኢትዮጵያን ማጥፋት የተሰኘውን የወያኔዎች ሰይጣናዊ ተግባር ነው። ከሁልም ግራ የሚያጋባውና የሚያሳዝነው ጉዳይ ደግሞ የህወሃት ተባባሪ ሆኖ አገሩ ኢትዮጵያን የሚያዘርፈውና የሚያጠፋው ወያኔ ያልሆነው ኢትዮጵያዊ ጉዳይ ነው። ሌላው ደግሞ ጉዳዮ አያሳስበኝም በማለት ከዳሮ ቆሞ ለግል ህይወቱ ወይም በሌላ ጉዳይ መላው ጊዜውን የሚያጠፋው ኢትዮጵያዊ ሁኔታም በጣም የሚያስተዛዝብ ነው። ከወያኔዎች ጋር በመተባበር አገሩን የሚያጠፋው ኢትዮጵያዊ ወንጀል ደግሞ እጅግ የሚያሳዝን ነው። ጊዜው ሳይጨልም ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር መቆም የወቅቱ እጅግ አንገብጋቢ ጥሪ ነው።

ዋናው የሚያሳስበው የአገር የቀጣይ የልማትና የህልውና ጉዳይ ነው። ከትግራይ በስተቀር አገሩን በሙሉ ለውጭ ባለሃብት ሽጦ እድገት ያመጣ አገር በአለማችን ላይ ታይቶ አይታወቅም። ትግራይ አትሸጥም የተቀረው ኢትዮጵያ ግን ማንም የሚገዛው ሸቀጥ ሆኖል። በፖሊሲ ራእይና ግብ እንኳን ከፍተኛ አድሎ አለ። በትግራይ ለመገንባት የታለመው የካፒታሊዝም ዓይነት አብዛኛውን ህዝብን ተጠቃሚ ሊያደርግ ይችላል ተብሎ የታለመው በልማታዊ መንግስት የሚመራ የቻይናንና የምስራቅ ኤሽያ አገሮችን የመሰለ በመንገግስታዊ ካፒታልዝም አካሄድ ለይ የተወጠነ ሲሆን። በተቀረው ኢትዮጵያ በመገንባት ላይ ያለው የካፒታሊስት ዓይነት ግን በዘረፋ ላይ የተመሰረተና አብዛኛውን አደህይቶ ጥቂቶችን ብቻ ሀብታም ሊያደርግ የሚችል ክሮኒ ወይም ብልሹ ካፒታሊዝም ነው። ይህ ደግሞ ለወያኔዎቹና ለሸሪኮቻቸው ለዘረፋ እንዲያመችና የተቀረው ኢትዮጵያውያንን ደሃ የሚያደርግና ኢትዮጵያንም እንዲያዳክም ሆን ተብሎ የተወጠነ የህወሃት ታላቁ ሴራ ነው። በአዲስ አበባ የሚደረገው ከፍተኛ የሕንፃ ግንባታማ ሆነ በአዲስ አበባ ከተማ ላይ በልመና የተሰማሩ ከትግራይ የመጡ የኔ ቢጤዎችን ማሳየት፤ እንዲሁም የዓባይ ግድብ ማዋለያ የህወሃትን ታላቁን ሴራ የመሸፋፈኛና የማደናገሪያ ዘዴዎች ናቸው። ትልቁን ምስል ወይም ትልቁን ዝሆን እንዳይታይ ለመሸፈን የማደናገሪያና ስልቶችና የህወሃትን ታላቁን የዘረፋ መንገድ ማራዘሚያ ዘዴዎች ናቸው። በሃያ ሰባት ዓመት ከሰላሳ ቢልዮን ዶላር በላይ የሰረቀን ሌባ አምስት ቢልዮኑን ቢመልስ እንኳን የሃያ አምስት ቢልዮን ዶላር ሌባ ይባላል እንጂ ሌብነቱ ሊዘነጋ አይቻልም። ሕዝቡ የህወሃት ዘራፊዎች በሚገባቸው ቋንቁ ብሶቱን እየገለፀ ስለሆነ ህወሃቶች ቀኑ ሳይጨልም የሕዝቡን መሠረታዊ የፍትህ ጥያቄ በትክክለኛ መንገድ ቢመልሱ የተሻለ ነው። ያለበለዚያ ግን የሚደርስባቸው አደጋ ከፍተኛ መሆኑ በቂ ምልክቶች በሚገባ እየታዩ ናቸው። ከአገር ቤትም ሆነ ከአለም አቀፍ አካባቢም የሚለገሰው ምክር ተመሳሳይ ነው። የኢትዮጵያ ህዝብ መብቱን ለማስከበር ቆርጦ ተነስቷል።

የአማራና የኦሮሞ ትብብር ይለምልም ፕሮጀክት ዓላማ በኦሮሞና በአማራ መሀከል ጎጂ ንትርክ ሳይሆን ጤናማ ውይይትና ትብብር የሚጎለብትበትን መንገድ የሚያበረታቱ ሀሳቦችን በማፈላለግና በማሰራጨት፤ በኦሮሞና በአማራ የፖለቲካ ልዒቃን መሀከል የሚደረገው ያለፈ ታሪክ ንትርክን በተመለከት የታሪክ ባለሙያዎች በሰለጠነ መንገድና በመከባበር እንዲወያዩበት የሚገባ መሆኑን እያበረታታ። በአሁኑ ወቅት የአማራና የኦሮም የፓለቲካ ልዒቃን በአንገብጋቢው የወቅቱ የፓለቲካ ጉዳይ ላይ በማተኮር የህወሃትን አገርንና ሕዝብን የሚያጠፋ ድርጊት ለመቋቋም የሚችሉበትን ጠንካራ ትብብር የሚፈጥሩ ጉዳዮች ላይ ትኩረት ማድረግ ነው።

የአማራና ኦሮሞ ትብብር ይለምልም ፕሮጀክት

AOCPP (Amhara and Oromo Cooperation Promotion Project)

Contact: aocpp2016@gmail.com

Hiber radio Las Vegas ይህ ህብር ሬድዮ _የወቅታዊ መረጃ ምንጭ ነው። ህብር ሬድዮ በአቤኔዘር ኮሙኒኬሽን ሴንተር እየተዘጋጀ  ከላስ ቬጋስ ከተማ፣ ዘወትር ዕሁድ በአካባቢው ሰዓት አቆጣጠር ከምሽቱ 630 ሰዓት እስከሰዓት በህብር ሬዲዮ ድህረ ገጽ ወይም በቀጥታ በስልክ ለማዳመጥ  5639993994 ወይም 563999-3988 ወይም 712-432-8451 በመረጡት ቁጥር መደወል ብቻ በቂ ነው በእንግሊዝ ለምትኖሩ 01405770140 በስልክ ማዳመጥ ይቻላል። ዘወትር በድህረ ገጻችን፣ googel app store Hiber Radio ወደ ስልክዎ በመጫን ካልሆነም በዘሐበሻ እንዲሁም በተጠቀሱት ስልኮች ማዳመጥ ይቻላል።

 

 

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *