Hiber Radio: የመኢአድ ፕሬዝዳንት አቶ ማሙሸት አማረ -መፈታቴ ደስተኛ የሚያደርገኝ አጠቃላይ ኢትዮጵያ ስትፈታ ነዉ

ሸንቁጥ አየለ

ልክ ከእስር ቤት እየወጣ ሳለ የመኢአድ ፕሬዝዳንትን አቶ ማሙሸት አማረን እንኳን ደስ አለህ ልለዉ ስልክ ደዉዬ ነበር:: የመለሰልኝ መልስ በጣም አስደመመኝ:: አሁንም ለትግል ያለዉ ወኔ አለመብረዱም ገረመኝ::ከአስራ ሶስት አመታት በላይ ሲታሰር ሲፈታ የኖረ ሰዉ አለወንጀሉ ታስሮ ሲፈታ ምን ሊሰማው እንደሚችል እኔ ማወቅ አልችልም:: ሆኖም እንኳን አብሮ ደስ ያለን ይለኛል ብዬ ነበር የጠበቅሁት::ሆኖም እሱ “መፈታቴ ደስተኛ የሚያደርገኝ አጠቃላይ ኢትዮጵያ ስትፈታ ነዉ” ብሎ መለሰልኝ:: ማሙሸት አማረ አስከትሎም የሚከተለዉን ተናገረ::

“ደስተኛ ልሆን የምችለዉ ሁሉም የመኢአድ አመራሮች እና አባላት ሲለቀቁ ነዉ:: ደስተኛ የምሆነዉ ሁሉም የተቃዋሚ ሀይላት ሲለቀቁ : ሁሉም የሰበአዊ መብት ታጋይ ሲፈቱ: ሁሉም ጋዜጠኞች ሲፈቱ ብሎም በመጨረሻ ዲሞክራሲ እና ሰላም የናፈቀዉ የኢትዮጵያ ህዝብ ዲሞክራሲን ሲጎናጸፍ ብሎም ኢትዮጵያ ወደ በለጸገ ሀገርነት ደርሳ ህዝቧ ደስተኛ ሲሆን ነዉ::መፈታቴ ደስተኛ የሚያደርገኝ አጠቃላይ ኢትዮጵያ ስትፈታ ነዉ::

አሁን እኔ ተፈታሁ ብዬ ደስታ የለኝ::ምን ደስታ ይኖረኛል? መጀመሪያዉንም የታሰርሁት ያለ ወንጀሌ ነዉ::ስለ ህዝቤ ዲሞክራሲ እና መብት በመታገሌ ብቻ ነዉ የታሰርኩት::

አሁን የእኔ መፈታት ህዝቤም አብሮ ዲሞክራሲን ካላገኘ ምንም ዋጋ የለዉም::የኔ መታሰር እና መፈታት ቁምነገር አይደለም:: ስታሰር እና ስፈታ የኖርኩት ለህዝብ ዲሞክራሲ እና ሰላም ነዉ:: እናም አሁን መፈታቴ ደስተኛ ሊያደርገኝ አይችልም::ምክንያቱም ህዝባችን ዲሞክራሲ: እና እፎይታን ገና አላገኘም እና::

መኢአድን በህጋዊነት ተመርጠን እየመራን ያለን በርካታ አመራሮች አለጥፋታችን ታስረናል::ተሰደናል::መከራ ተቀብለናል::የተገደሉብንም አሉ:: ባለን ያልተጣራ መረጃ መሰረትም ከ120 በላይ የመኢአድ አመራሮች ታስረዋል::እጅግ በርካታ የመኢአድ አባላት እስር ቤት ናቸዉ:: አሁንም በርካታ አመራሮቻችን እና አባላታችን እንደታሰረ ነዉ:: እጅግ ብዙ ተቃዋሚ እና የሰበአዊ መብት ታጋይ እና ጋዜጠኞች እስር ቤት ናቸዉ:: እንደ እኔ እስር ቤቱን አይቶት የወጣ ሰዉ ይሄ ሁሉ ወገን ታስሮ ሳለ ምንም ደስተኛ ሊሆን አይችልም:: አጠቃላይ ኢትዮጵያ ከእስር መፈታት አለባት::ያኔም ህዝባችን ደስተኛ ሲሆን: ዲሞክራሲ ሲሰፍን እና ብልጽግና ያለዉ ማህበረሰብ ሲኖረን ከህዝባችን ጋር ደስተኛ እንሆናለን::”

የምታስተላልፈዉስ መልዕክት አለህ? ስል ጠየቅቅሁት::ፈጠን ብሎ ሶስት ነገሮችን እንደሚከተለዉ ተንትኖ አብራራልን::

1ኛ. ኢህአዴግ አሁን ያለዉ ብቸኛ አማራጭ አጠቃላይ እስረኞችን በመፍታት: የሽግግር መንግስት ተቋቁሞ ፍትሃዊ ምርጫ እንዲደረግ በማድረግ ኢትዮጵያ ወደ ዲሞክራሲና መረጋጋት እንድትገባ ማድረግ መሆኑን መረዳት አለበት::

2ኛ. ተቃዋሚዎች እዚህ እና እዚያ ተበታትነን አሁንም በደካማ አካሄድ ህዝብ እንመራለን የምንለዉን አካሄድ ትተን: ትናንት የገባንበትን መቃቃር አስወግደን አብረን በመስራት የኢትዮጵያ ህዝብ እፎይታ የሚያገንበትን እና ዲሞክራሲን የሚጎናጸፍበትን ሂደት ማፋጠን አለብን::

3ኛ. አስመሳይ ተቃዋሚዎች ከአምባገነኖች ጋር በመሞዳሞድ: የአምባገነኖች ሰላይ በመሆን እና እዉነተኛዉን ትግልን ጠልፎ በመጣል የሚያደርጉትን ጸረ ህዝብ አካሄድ እንዲተዉ መገደድ አለባቸዉ:: የኢትዮጵያን ህዝብ የዲሞክራሲ ትግል ማዳከም እና ማጓተት በህዝብ እንደሚያስጠይቃቸዉ ማወቅ አለባቸዉ::

Hiber radio Las Vegas ይህ ህብር ሬድዮ _የወቅታዊ መረጃ ምንጭ ነው። ህብር ሬድዮ በአቤኔዘር ኮሙኒኬሽን ሴንተር እየተዘጋጀ  ከላስ ቬጋስ ከተማ፣ ዘወትር ዕሁድ በአካባቢው ሰዓት አቆጣጠር ከምሽቱ 630 ሰዓት እስከሰዓት በህብር ሬዲዮ ድህረ ገጽ ወይም በቀጥታ በስልክ ለማዳመጥ  5639993994 ወይም 563999-3988 1641-793-8229 ወይም 1641-715-8596  በመረጡት ቁጥር መደወል ብቻ በቂ ነው በእንግሊዝ ለምትኖሩ 01405770140 በስልክ ማዳመጥ ይቻላል። ዘወትር በድህረ ገጻችን፣ googel app store Hiber Radio ወደ ስልክዎ በመጫን ካልሆነም በዘሐበሻ እንዲሁም በተጠቀሱት ስልኮች ማዳመጥ ይቻላል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *