የኢትዮጵያ ህግ ልዕልና ከአሜሪካ ፕሬዘዳንት ክብር በላይ ሊሆን ይገባዋል !

Obama_01

የኢትዮጵያ ነጻ ፕሬስ ጋዜጠኞችን “አሸባሪዎች” ብሎ በማሰር እና ከአገር እንዲሰደዱ በማድረግ የኢህአዴግ መንግስት ያላቋረጠ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን ሲፈጽም ቆይቷል። ይህን የሰብአዊ መብት መተላለፍ በመቃወም፤ በአገር ውስጥ እና በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ድምጽ ለሌላቸው ድምጽ በመሆን ወገናቸን ታድገዋል። ሃሳባቸውን በነጻነት በመግለጻቸው ብቻ፤ “አሸባሪ” ተብለው በእስር ሲማቅቁ ከነበሩት ጋዜጠኞች እና ጦማርያን መካከል ተስፋለም ወልደየስ፣ ዘላለም ክብረት፣ አስማማው ሀ/ጊዮርጊስ፣ ርዕዮት አለሙ፣ ማህሌት ፋንታሁን እና ኤዶም ካሳዬ ተፈትተዋል።

የእነዚህ ነጻ ጋዜጠኞች እና ጦማርያን መታሰር ከልብ አሳስቧቹህ፣ በማበራዊ ድረ ገጾች፣ በጽሁፍ፣ በቃል እና በሰላማዊ ሰልፍ ጭምር ድምጻቸውን ያሰማችሁላቸው በሙሉ፤ እነሆ የአምላክ ፈቃድ ሆኖ ድምጻቹህ ተሰምቷል። ጋዜጠኞቻችን በከፊል ተፈተዋል። ሆኖም ዛሬም ቢሆን ሰባት ጋዜጠኞች እና ጦማርያን፤ “አሸባሪዎች” ተብለው ክስ ተመስርቶባቸው፤ ከአመት በላይ በእስር ላይ በመማቀቅ ላይ ናቸው። እነዚህ ጋዜጠኞች፡

1- እስክንድር ነጋ 2- ውብሽት ታዬ 3- ተመስገን ደሳለኝ 4- አቤል ዋበላ 5- ናትናኤል ፈለቀ 6- በፍቃዱ ሃይሉ 7- አጥናፍ ብርሃኔ ሲሆኑ፤ ከሙስሊሙ ህብረተሰብ ጋር ደግሞ – ያሲን፣ የሱፍ ጌታቸውና አቡበኩር አለሙ የተባሉት ጋዜጠኞች “አሸባሪ” ተብለው ታስረዋል። እነርዕዮት አለሙ በተፈቱበት ምሽት ደግሞ ጋዜጠኛ ሃብታሙ ምናለ ከቤቱ ታፍኖ ተወስዶ፤ በእስር ላይ ይገኛል።

በኢትዮጵያ ሰላማዊ ትግል እና ሃሳብን በነጻነት መግለጽ በጨለማ ውስጥ እንደሚበራ ጭላንጭል የጧፍ መብራት ነው። ኢህአዴግ – ይህን በሚሊዮኖች መስዋዕትነት የተገኘ የነጻነት ጭላንጭል ካዳፈነው፤ የህዝቡ ቀጣይ አማራጭ አመፅ እና የትጥቅ ትግል መሆኑ በተግባር እየታየ መጥቷል።

ከኢትዮጵያዊነት ባህል ውጪ የሆነውን፤ አሸባሪ ህግ አርቅቆ እና በአዋጅ አሳውቆ – የኢህአዴግ ተቃዋሚን “አሸባሪ” ብሎ የማሰር መጥፎ ባህል ከስሩ ሊነቀል ይገባዋል። ይህ ካልሆነ – በአገሪቱ ውስጥ እየታየ ያለው የጦርነት ጭስ፤ ሰላማዊውን ሰማይ ሙሉ ለሙሉ ሳያጠቁረው በፊት፤ ሌሎች የፖለቲካ ድርጅት መሪዎች እና የሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባሎችን በመፍታት ውጥረትን ማርገብ ብልህነት ነው። ይህ ካልሆነ ግን ያለወንጀላቸው “አሸባሪ” ተብለው በእስር ላይ ለሚገኙት ዜጎችን ሲሉ፤ እሳት ለመጨበጥ የጨከኑ እጆች መኖራቸውን መዘንጋት ከታሪክ አለመማር ይሆናል።

በአጠቃላይ ጋዜጠኞች ሃሳባቸውን በጽሁፍ ስለገለጹ፤ በአሸባሪነት ታስረው ቆይተዋል። ቀሪዎቹም ለአሜሪካ ፕሬዘዳንት ክብር ተብሎ ሳይሆን፤ ስለህግ እና ፍትህ ልዕልና ሲባል – ሊፈቱ ይገባል።

በመጨረሻም – በአሁኑ ወቅት ከእስር ለተፈቱት ጋዜጠኞች እና ቤቴቦቻቸው፤ “እንኳን ደስ አላቹህ” እያልን፤ እስር ቤት የተውናቸውን ዜጎች ነጻ የማውጣቱ ሰላማዊ እንቅስቃሴ ተጠናክሮ እንዲቀጥል፤ በዚህ አጋጣሚ ጥሪያችንን እናቀርባለን።

በስደት የሚገኙ የኢትዮጵያ ነጻፕሬስ ጋዜጠኞች

 

 

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *