Hiber Radio: የቆሼው እልቂት ድንገተኛ አደጋ ወይስ የመንግሥት ሴራ? – ዘመድኩን በቀለ | ሊያነቡት የሚገባ አዳዲስ መረጃዎች

በተለምዶ ቆሼ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ የከተማዋ የአዲስ አበባችንን ቆሻሻ በዚያ ስፍራ መጣል ከተጀመረ 50 ዓመታት እንዳለፉት መረጃዎች ያመለክታሉ ። እንደ ሰለጠኑት ዓለማት ቆሻሻን መድፋትና በአንድ ቦታ መከመር እንጂ ቆሻሻን ሰብስቦ ለልማት ለማዋል በየግዜው ሀገሪቱን የመግዛት ዕድሉን ባገኙት ገዢዎችን በኩል ፈቃደኝነቱም ሆነ ተነሳሽነቱ እንደሌለ ይታወቃል ።

የሆነው ሆኖ ከዛሬ 50 ዓመት በፊት ከአዲስ አበባ ከተማ ውጪ ነው የተባለ የቆሻሻ ማጠራቀሚያ ስፍራ ዛሬ ከህዝቡ መብዛትና ከከተማዋ መስፋፋት ጋር ተዳምሮ የቆሻሻ መጣያ ስፍራው የከተማዋ እንብርት የሆነ ሥፍራ ላይ ራሱን እንዲያገኝ ጊዜ ግድ ብሎታል ።

ኢህአዴግ ከ97 ቱ ምርጫ በኋላ በከተማዋ ነዋሪዎች የደረሰበትን ክፉኛ የሆነ ሽንፈት ለመቀልበስና የሕዝቡንም ልብ ወደ ቀልቡ ለመመለስ ሲል ከ15 ዓመት እንቅልፍ በኋላ በሀገራችን ከዚህ ቀደም ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ የከተማ ልማት ፖሊሲን በመቅረጽ የእውር ድንብሩን ሥራ መጀመሩን እናውቃለን ። ኮንዲሚንየም ፣ ባቡር የመሳሰሉትን ልማቶች ህዝቡ አገዛዙን እጁን በመጠምዘዝ በግድ ያመጣው መሆኑም ይታወቃል.? ወዘተ

የሆነው ሆኖ በቆሼ ከከተማዋ ነዋሪ ብዛት የተነሳ በሥፍራው የሚጣለው ቆሻሻ ወደ ተራራነት ከመቀየሩም ሌላ ከቆሻሻው የሚወጣው መጥፎ ጠረን ፤ እንኳን በዚያ አካባቢ ሊያስኖር ይቅርና በአካባቢው በሚገኘው የቀለበት መንገድ ላይ በፍጥነት እያሽከረከሩም ሊያልፉ ቢሞክሩ ሽታው ጥርቅም ብሎ በተዘጋ መስኮት ገብቶ ለበሽታ የሚዳርግ መጥፎ ጠረን መማጎት እንደሁ የማይቀርበት ስፍራም ነው ። ቆሼ ።

መንግሥት የቆሻሻ መጣያ ሥፍራውን ከአዲስ አበባ ክልል በማውጣት ወደ ኦሮምያ ክልል ወስዶ ቦታውን በማጽዳት ልማት ላይ ማዋል እንደሚፈልግና በዚህም በኩል ሰፊ የሆነ እንቅስቃሴ መጀመሩንም በሚድያዎቹ አማካኝነት ከነገረንም ቆይቷል ። በዚህም መሠረት በሥፍራው ላይ የባዮ ቴክኖሎጂ ፋብሪካ በማቋቋም እንዲያውም ከቆሻሻው በሚወጣ ኃይል የኤሌክትሪክ ኃይል ለማመንጨት ጭምር ቅድመ ዝግጅቱን ጨርሶ ወደ ትግበራ ለመግባት ይፋ አድርጎልን ነበር ።በዚህ በኩል የተከበሩ Eshetu Homa Keno መረጃዎችን በመጎልጎል ቢተባበሩን ምንኛ ያማረ እንደሚሆን አትጠይቁኝ

በዚህም ምክንያት በቆሼ አካባቢ ለተወሰኑ ጊዜያት ቆሻሻ መድፋትም እንዲቆምም ተደርጎ ነበር ። በቆሼ አካባቢ የሚኖሩ ነዋሪ ዜጎችም የቆሼ አስቀያሚ ሽታ ባይጠፋላቸውም በመጠኑም ለጥቂት ጊዜም ቢሆን እፎይታን አግኝተው እንደነበር ነዋሪዎቹ ይናገራሉ ። ነገር ግን በኦሮሚያ የሚጣለው የአዲስ አበባ ቆሻሻ ቆሻሻ በክልሉ ተቃውሞ ከተነሳባቸው አንዱ ምክንያት የነበረው ይህ ጉዳይ በመሆኑም ፤ መንግሥት ሳይወድ በግዱ በድጋሚ ፊቱን ወደ ቆሼ ለማዞር ተገደደ ።

አሁን ቆሼ የከተማዋ የአዲስ አበባ እንብርትና ለመሬት ነጋዴው መንግሥታችን ደግሞ ሽንኩርት የሆነ ሥፍራም ነው ። እናም መንግሥት ሆዬ ቆሼ የተባለውን ሥፍራ ቸርችሮ ለመሸጥ ምራቁን አዝረብርቦ እንደጎመዠበት የተገለፀ ሀቅም ሆነ ፣ ይህን በካሬ ሜትር ሲቸበቸብ እንደ ሜሪኩሪ ሽያጭ ብር የሚዛቅበትን ስፍራም አጽድቶ ለመረከብም ቋመጠ፣ ተቁነጠነጠም ። ነገር ግን በፈለገው ሰዓት መሬቱን እንዳይረከብ ጋሬጣ ከፊቱ ተጋረጠበት ። ይኽ ጋሬጣም ድኅነት አሯሩጦ መኖሪያቸውን ከቆሻሻ ሥር ቆሻሻ እያሸተቱ እንዲኖሩ የፈረደባቸውና በህጋዊ መንገድ ካርታ ከመንግሥት ተሰጥቷቸው ጎጆ ቀልሰው በአካባቢው የሚኖሩት ምስኪን ዜጎችን ነበሩ ። እነዚህን ዜጎች እንዴት ከዚህ ስፍራ እንደሚያስነሳቸው መምከር የያዘውም ወዲያው ነው ።

ኢህአዲግ ሆዬ ቋምጦም አልቀረ በኮልፌ ቀራንዮ አስተዳደር በኩል ከ400 በላይ አባወራዎችን በመሰብሰብ ” ቦታው ለልማት ስለተፈለገ በአስቸኳይ ልቀቁ ” የሚል መመሪያና ትእዛዝ መሰል ነገር ለነዋሪዎቹ ይነገራቸዋል ። ነዋሪዎቹም በበኩላቸው ልማቱን እንደማይቃወሙ እንዲያውም ከዚህ አሰቃቂና አስከፊ ስፍራ ለቆ መሄድ የሚጠቅመው ራሳቸውን በመሆኑ የልማቱ አጋር መሆናቸውን ለክፍለከተማው አስተዳደር ይነግራሉ ። ነገር ግን ከቦታው ለመነሳት ተገቢ ካሳና ምትክ የሆነ መሬት ከተሰጣቸው ከቦታው ለመነሳት ነገ ዛሬ ሳይሉ በፍጥነት እንደሚነሱ ጭምር ፈቃደኝነታቸውን በመግለጽ አቋማቸውን ለመንግሥቱ ይገልጻሉ ።

የከተማው አስተዳደርም መልሶ ለዜጎቹ አስደንጋጭ የሆነ እና ተሰምቶ የማይታወቅ ምላሽ ይሰጣቸዋል ። ” ምትክ ቦታም ሆነ የምሰጣችሁ ገንዘብ የለኝም ” በማለት ለነዋሪዎቹ በመግለጽ ያም ሆነ ይህ ግን ከቦታው በአስቸኳይ እንዲነሱ መወትወቱንና ማስፈራራቱን ቀጠለ ። ነዋሪዎቹም አሁንም ቢሆን ከኖሩት በታች ከሞቱት በላይ ስለሆንን የፈለጋችሁትን አምጡ በማለት በእንቢተኝነታቸውና በአቋማቸው ይፀናሉ ።

እስከዚህ ድረስ ያለውን እና ቀጥሎ ያለውንም ነገር የሚነግረኝ በቆሼ አደጋ ይቅርብ ዘመዱን ያጣና ከአደጋ የተረፈ ወዳጄ መሆኑን ልብ ይሏል ።

 

ከዚህ በኋላ ነው እንግዲህ እንዲህ ሆነ ። መረጃውን የሰጠኝ ወዳጄ ትረካውን ይቀጥላል ።

እኔም በትረካው መሃል ጥያቄዬን አቀርባለሁ ። ጥያቄዬም በግልጽ ለህወሓት የሚቀርብ ነው ። ኢህአዲግ የካሴቱ ከቨር ስለሆነ ለመመለስ ይቸገርብኛል ብዬም ነው ። እንቀጥል ።

፩ኛ ፦ የቆሼ የተራራ ክምር ከመደርመሱ በፊት ሐሙስ ቀን ማለት ነው ያለወትሮው አንድ ኦራል ሙሉ መኪና የመከላከያ ሠራዊት እና የፌደራል ፖሊስ የደንብ ልብስ የለበሱ ወታደሮች የቆሻሻ ተራራውን ዙሪያ ከበብው ቆሙ ። መቆሙን ይቁሙ ጥያቄው ለምን ቆመው ውለው አደሩ.?

፪ኛ፦ በቀጣዩ አርብ ቀን መከላከያና ፌደራል ፖሊሶቹ ሥፍራውን ለቅቀው በምትኩ የቆሼ ዙሪያ በከተማዋ ፖሊስ እንዲከበብ ተደረገ ። ለምን ተደረገ.?

፫ኛ ፦ ይሄ ሁሉ ሲሆን ማንኛውም ሰው ቆሼን አቋርጦ እንዳይሄድ ለምን በፖሊሶቹ ተከለከለ.? ለምን ተከለከለ? ። አሁን ጥርጣሬው ከፍ ይልና ወለል ያለ ምስል ይፈጠርልናል ።

፬ኛ፦ በምስኪኖቹ የቆሼ ነዋሪ ቤቶች ላይ የቆሻሻ ክምሩ ከመናዱ በፊት የተሰማው ከባድ የፍንዳታ ድምጽ ተከሰተ ። ይህ የከባድ ፍንዳታ ድምጽ ከየት የመጣ ነው ? ይሄንን ዜና ቤተሰባቸውን በሙሉ በአደጋ ያጡ አንዲት እናት ለአሜሪካ ድምጽ ራዲዮ መናገራቸው ልብ ይሏል ።

፭ኛ ፦ መቼም የመከላከያና ሠራዊቱና የፌደራል ፖሊሶቹ ቆሼን ከበው ሲከርም ነዳጅ እየቆፈሩ ነበር እንደማንባል እርግጠኛ ነኝ ።

፮ኛ፦ ለወትሮው አደጋ በደረሰበት ሥፍራ በቶሎ የማይገኙት የከተማዋ የፖሊስ ሠራዊት አባላት የዚያን ዕለት በዚያ ፍጥነት እልፍ አእላፋት ሆነው በዚያ ቁጥር እንዴት በስፍራው ሊፈስሱ ቻሉ.?

፯ኛ፦ አደጋው እንደደረሰ የአካባቢው ነዋሪዎች የነፍስ አድን ሥራ ለምሥራት ሲንቀሳቀሱ በፖሊሶቹ ለምን ተከለከሉ.?

፰ኛ፦ ከሁለት ሰው ቤት ውስጥ እንኳን 16 ሰዎች መሞታቸውን እያየን እና እየሰማን ከዚያ ሁሉ ሰው መኖሪያ ቤት ውስጥ የሟቾችን ቁጥር በ60 እና 70 ወስኖ መናገሩስ የጤና ነውን? ። ለነገሩ መንግሥት በቁጥር በኩል 60 ነው ካለ ትክክለኛውን ቁጥር ለማወቅ 60ን በ20 እና በ30 ማባዛት ብቻ ነው ።

እንግዲህ እኔ በአካባቢው አደጋው ከደረሰበት ሥፍራ የተረፈ ዜጋ ስለ አደጋው ሲያጫውተኝ ወደ አእምሮዬ የመጣ ጥያቄ ነው ያቀረብኩት.? እንዲያው መንግሥቱ ምላሽ ይሠጠኛል ብዬ ሳይሆን እንዲሁ ለጫወታ ያህል መጠየቄ ነው ።

✔ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳዋል እንዲሉ በነገራችን ላይ እግረ መንገዴን ሌላ ጥያቄ መጠየቅ ስላማረኝ ጠይቅ ጠይቅም ስላለኝ ሌላ ጥያቄ ልጠይቅ ።

፩ኛ፦ እኔ የምለው ወገኖች ሲጎዱ 10 ሚልየን ብር መዥረጥ በማድረግና በመርዳት የሚታወቀው የሶማሌ ክልል መንግሥት አሁን ምነው ድምፁ ጠፋ.?

፪ኛ፦ ለአዝማሪ እና ለአንዳንድ ጋለሞታ የፊልም አክተሮችና ሞዴላ ሞዴሎች ቪላ ቤትና ሚልዮን ብር በማደል የሚታወቁት ሼካችን ይህን አደጋ አልሰሙ ይሆን? ደሃ እንደሚያፀዱ እንጂ እንደሚረዱ ባውቅም ጥያቄ መጠየቅ መብቴ ስለሆነ ነው እንዲህ መጠየቄ ።

፫ኛ፦ የምንወደው ሕዝባችን እያሉ ዘውትር በስሙ እየማሉ ሀብታም የሆኑት አርቲስቶቻችን መሬት ለሚሰጣቸው ክልል ካልሆነ በቀር አጋርነታቸውን ለቆሼ ሰዎች ለማሳየት ለምን አልፈቀዱ ይሆን.?

 

፬ኛ፦ እነዚያ ርኹሩኽና አዛኝ ለህዝባቸውም የሚንሰፈሰፍ አንጀት ያላቸው ቅዱሳን የሃይማኖት አባቶቻችንስ ተጎጂዎችን ከቦታው ድረስ ሄደው ለማጽናናት ያልደፈሩት ቦታው ርቆባቸው ይሆን.? ወይስ የቆሼ ሽታ ስኳርና አስማቸውን እንዳይቀሰቅስባቸው ሰግተው.?

አረ እኔስ እንደው ምን አይነት እና ምን የሚሉት ቀባጣሪ ነኝ በእናታችሁ ። አሁን እኔ ምን አገባኝ እና ነው እስኪ አሁን ከመሬት ተነስቼ የማይመለስ ጥያቄ ይዤ የምቀባጥረው.? አረ ምን አይነቱ ቀባጣሪ ነኝ በማርያም ። አረ አፉ በሉኝ ወዳጆቼ! ሆሆይ!

ቆሼ ድህነት ማለት ምን ማለት እንደሆነ በግልጽ የሚታይበት ሥፍራ ነው ። ቆሼ እነ አላሙዲን ጠግበው የደፉትን የምግብ ትራፊ ክቡር የሆነ የሰው ልጅ በህይወት ለመኖር ሲል ከውሻ ጋር እየተጋፋ የሚጠነባ ቆሻሻና ግማት የሰው ልጅን ከማያስቀርብ የቆሻሻ ገንዳ ውስጥ ትራፊ እየለቀሙ የሚኖሩበት ስፍራ ነው ። ቆሼ እውነተኛውን የኢትዮጵያን 11% ከመቶውን የእድገት ደረጃ የምናይበት ሥፍራ ነው ።

የሚያሳዝነው በቆሼ ዜጎች እንደ ቆሻሻው እነሱም ቆሻሻ ለብሰው ፣ ቆሻሻውን ምግብ አድርገው ፣ ቆሻሻው ላይ መኖሪያቸውን ሠርተው ፣ በመጨረሻም በቆሻሻው ሥር በቁማቸው እንዲቀበሩ እና በቆሻሻ ክምር እንዲወገዱ ተደረጉ ። ነፍስ ይማር ምስኪን ወገኖቼ.!

ይሄ የዘር ማጥፋት ድርጊት ነው ። ለጥፋቱ ተጠያቂው የሚሆነው የኢትዮጵያ መንግሥት ነው ። በኢህአዴግ ታሪክ አደጋ በደረሰበት ሥፍራ በመገኘት ዜጎችን ማጽናናት ፈፅመው የማያውቁት የከተማው ከንቲባ በአደጋው ሥፍራ መገኘት በራሱ ሌላ ጥያቄ የሚፈጥር ነው ። ከንቲባ ድሪባ አደጋው በደረሰበት ሥፍራ ተገኝተው የአዛኝ ቅቤ አንጓችነትን ሥራና የማስመሰል ድራማ ሠርተው እንዲሄዱ ተደርጓል ። አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝም የኃዘን ስሜት ተሰምቶኛል አይነት ጫወታ እንዲጫወቱ ተገድደዋል ። ምክርቤቱም ወድዶ ሳይሆን በግዴታው የ3 ቀን ብሔራዊ የሐዘን ቀን ማወጁን አይተናል ።

አሁንማ በየሳምንቱ ሳይሆን በተለያየ ምክንያት ለሚሞተው እና ለሚገደለው ህዝብ በየዕለቱ የሐዘን ቀን ሊታወጅ ባንዲራም ዝቅ ሊል ነው ማለት ነው ።

አሁን ቦታው ጸድቷል ። የካሳ ክፍያ የሚጠይቁ ዜጎች ቁጥርም ከነዘር ማንዘራቸው እንዲወገዱ ተደርጓል ። አሁን ልማታዊው መንግሥታችን በድሆቹ ሬሳ እና በድሆቹ ደም ላይ የፈለገውን አይነት ልማት መገንባት ይችላል ። ካሬ ሜትሩ በሚልየን ብርም መቸብቸቡ ቀጣዩ የእነ ሪፖርተር ጋዜጣ ዜናም እንደሚሆን ይጠበቃል ።

ነገር ግን የድሆች ደም በእግዚአብሔር ዘንድ ዋይ ዋይ ይላል ። የአቤል ደም እሪሪሪ ብሎ ይጮኻል ።እናም ጓደኞቼ መንግሥትም ከኦሮምያ ክልል በተነሳበት ተቃውሞ ምክንያት አዲስ አበባን ወደ ጎን ማስፋቱን ትቼ ውስጧን በማጽዳት ልማቴን አካሄዳለሁ ብሎ በተናገረው እቅድ ምክንያት የማጽዳት ሥራውን በዚህ መልኩ ጀምሮታል ። ነገ ደግሞ ተረኛው የትኛው ሰፈር ይሆን.? እሳት የሚለቀቅበት ፣ ድማሚትም የሚቀበርበት? የሚለውን ጥያቄ እየጠየቅን ለጊዜው እንሰነባበት.?

በቀጣይ በኢትዮጵያ የአንድ ብሔር ወይም ጎሳ ሕጻናትን መንግሥታችን እንዴት ለበሽታ እየዳረገ እንደሆነ የሚያሳይ መረጃ እጄ ገብቷልና እሱን እስካቀርብላችሁና ለመወያየት እስክንችል ድረስ ግን በቸር ቆዩኝ ጓደኞቼ ።

ይኽንንም ራሴው ዘመድኩን በቀለ ጻፍኩት ። +4915217428134 ደግሞ የቫይበር ፣ የኢሞና የኋትስአፕ መልእክቶችን የምቀበልበት የእጅ ስልኬ ነው ።

ሻሎም. ! ሰላም. !

ዘመድኩን በቀለ ነኝ ።

መጋቢት 7/ 2009 ዓም

ከራየን ወንዝ ማዶ

Hiber radio Las Vegas ይህ ህብር ሬድዮ _የወቅታዊ መረጃ ምንጭ ነው። ህብር ሬድዮ በአቤኔዘር ኮሙኒኬሽን ሴንተር እየተዘጋጀ  ከላስ ቬጋስ ከተማ፣ ዘወትር ዕሁድ በአካባቢው ሰዓት አቆጣጠር ከምሽቱ 630 ሰዓት እስከ 8 ሰዓት በህብር ሬዲዮ ድህረ ገጽ ወይም በቀጥታ በስልክ ለማዳመጥ 5639993994 ወይም 563999-3988 ወይም 712-432-8451 በመረጡት ቁጥር መደወል ብቻ በቂ ነው በእንግሊዝ ለምትኖሩ 01405770140 በስልክ ማዳመጥ ይቻላል። ዘወትር በድህረ ገጻችን፣ googel app store Hiber Radio ወደ ስልክዎ በመጫን ካልሆነም በዘሐበሻ እንዲሁም በተጠቀሱት ስልኮች ማዳመጥ ይቻላል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *