Hiber Radio:ኮ/ል ደመቀ ዘውዱና በሀሰት የተጠቀሰባቸው መዝገብ ቁጥር 104025 አስገራሚው ፋይል በጋዜጠኛ ጌታቸው ሽፈራው

 

ኮ/ል ደመቀ ዘውዱ የእሳቸው መዝገብ ነው የተባለው የሌላ ሰው መዝገብ (የሀሰት ማስረጃ) እንዲጣራላቸው ያቀረቡት አቤቱታ!

~መዝገቡ ከ2003 በፊት በሌላ ሰው ላይ የተከፈተ መዝገብ ነው! በ2004 ዓም ውሳኔ አግኝቷል። በእነ ኮሎኔል ደመቀ ላይ ይህ መዝገብ ተከፈተ የተባለው ከተዘጋ ከ3 አመት በኋላ ነው!

~ በፍርድ ቤት ትዕዛዝ የእነ ኮ/ል ደመቀ የስልክ ንግግር ተጠለፈ የተባለው ትክክል አይደለም። ዳኛው አዘዋል የተባለው ሕጋዊም እውነትም አይደለም! የማመልከቻውን ዝርዝር ከስር ይመልከቱ!

ለአማራ ክልል ጠ/ፍርድ ቤት

ጎንደር ምድብ ችሎት

ጎንደር

ከሣሽ :_ የፌ/ጠ/ዐ/ሕግ

ተከሳሽ:_ ኮ/ል ደመቀ ዘውዱ አየለ፣ አድራሻ ጎንደር ማረሚያ ቤት

ጠበቆች:_ አለልኝ ምህረቱ እና መክት ካሣሁን

ጉዳዩ:_ የማስረጃ ሀሰተኝነት እንዲረጋገጥ ስለመጠየቅ!

የፌደራል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ህዳር 15/2010 ዓም ከተፃፈ ማመልከቻ ጋር በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት መዝገብ ቁጥር 104025 ነሃሴ 25 ቀን 2007 ዓም ተሰጠ የተባለ የምርመራ ፈቃድ ትዕዛዝ ግልባጭ አቅርቧል። ሆኖም ይህ የፍርድ ቤት ትዕዛዝ ነው የተባለው ሕጉን ያልተከተለ ከመሆኑም በተጨማሪ ሀሰተኛ ሰነድ መሆኑን አረጋግጠናል።

1) ስለሕጋዊነቱ:_

የፌደራል ፍርድ ቤቶች ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 25/88 አንቀፅ 23 በአዋጅ ቁጥር 454/97 አንቀፅ 23(3)(ሀ) መሰረት እንደተሻሻለ ከ15 አመት በላይ የሚያስቀጡ ወንጀሎች በ3 ዳኞች እንደሚታዩ ደንግጓል። በተጨማሪም የፌደራል ፍርድ ቤቶች ፕሬዝደንቶች እና ም/ፕሬዝደንቶች በ3 ዳኞች በሚታዩ ጉዳዮች በሰብሳቢነት ከሚሰሩ ውጭ በመደበኛ ዳኝነት እንዲሰሩ አልተፈቀደላቸውም። አሁን የቀረበው ሰነድ በአንድ ዳኛ ብቻ የታየ ከመሆኑ በላይ በዳኝነት ተሰየሙ የተባሉት አቶ ሀብቴ ፍቻለ በዚህ ወቅት ከቦታው የነበሩ ስለመሆኑ የሚጣራ ቢሆንም በቦታው በነበሩ ጊዜ ይሰሩ የነበረው በዳኝነት አስተዳደር ዘርፍ (በምክትል ፕሬዝደንትነት) እንደነበር አረጋግጠናል።

2) በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሆነ የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤቶች የመዝገብ ቁጥሮች በወንጀልም ሆነ በፍትሕብሔር ጉዳዮች ቁጥራቸው ተከታታይ ነው። ማለትም የወንጀል መዝገብ ቁጥሮች እና የፍትሕብሔር መዝገብ ቁጥሮች ከተራ ቁጥር 1 ጀምሮ በተከታታይነት ስለሚመዘገቡ ተመሳሳይ ቁጥር የሚይዙበት አጋጣሚ የለም። በዚህም መሰረት በመዝገብ ቁጥር 104025 በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የተመዘገበው በከሳሽ ጉለሌ ክፍለ ከተማ ቀበሌ 07/17 እና በእነ አስረስ ተካልኝ መካከል የነበረ የፍትሕብሔር ክርክር ሲሆን በ10ኛ ፍትሕብሔር ችሎት ለረዥም ጊዜ ሲታይ ቆይቶ ከነሃሴ 25/2007 ዓም በፊት ከሶስት አመት ከአራት ወር ቀደም ብሎ ሚያዝያ 25/ቀን2004 ዓም ውሣኔ ያገኘ መዝገብ ነው።

3) ከላይ የተጠቀሰውን እውነታ ለማረጋገጥ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት በታህሳስ ወር 2007 ዓም ላይ የመዝገብ ቁጥር 161802 ደርሶ ነበር። አሁን ነሃሴ 25 ቀን 2007 ዓም ተሰጠ የተባለው ትዕዛዝ ደግሞ ከላይ ከተጠቀሰው መዝገብ በኋላ 8ወር ቆይቶ ከተከፈተ በታህሳስ 2007 ዓም ከተከፈተው መብለጥ እንጅ ማነስ ያልነበረበት ሲሆን ይልቁንም ከመዝገብ ቁጥር 161802 ላይ 104025 ሲቀነስ በ57,777 መዝገቦች አንሶ ይገኛል። እውነታው ደግሞ ዐቃቤ ሕግ በማስረጃነት ያቀረበው መዝገብ ቁጥር ከ2003 ዓም በፊት የተከፈተ የፍትሕብሔር መዝገብ መሆኑን በፍርድ ቤቱ ዳታ ቤዝ አረጋግጠናል።

ስለዚህ በክርክር ሂደት በሚመጡ አዲስ ጭብጦች የሚፈለጉ ማስረጃዎች ካልሆኑ በስተቀር ከጉዳዩ ጋር ተያያዥነት ያላቸው ማንኛውም የወንጀል ማስረጃዎች በወንጀለኛ መቅጫ ሕግ ሥነ ሥርዓት ቁጥር 98 መሰረት አስቀድሞ መያያዝ የነበረባቸው ሲሆኑ ይህ ማስረጃ አስቀድሞ ያልተያያዘው ያልነበረ ስለሆነ የተከሳሽ ስልክ እንዲጠለፍ ትዕዛዝ ተሰጠ የተባለበት መዝገብ በ2004 ዓም ውሣኔ ያገኘ የፍትሕብሔር መዝገብ ስለሆነ ይህ ማስረጃ ሀሰተኛ መሆኑ ደግሞ ሌሎች ማስረጃዎችም ተመሳሳይ እንዲሆኑ ሙሉ ግምት ሊያስወስድ የሚችል በመሆኑ የፌደራል ከፍ/ፍ/ቤት ልደታ ምድብ ችሎት ሬጅስትራል ፅ/ቤት የተጠቀሰው መዝገብ ቁጥር በማን ስም እንደሆነ እንዲያረጋግጥ እንዲታዘዝልኝ በትህትና አመለክታለው!

ስለ ተከሳሽ

ጠበቃ አለልኝ ምህረቱ

(በዚህ ማመልከቻ መሰረት መዝገቡን እንዲልክ በአማራ ጠ/ፍ/ቤት ትዕዛዝ የተሰጠው ልደታ ከፍተኛ ፍርድ ቤት መዝገቡን ሳይልክ ቀርቷል። ይህ ማመልከቻ የተፃፈው ሕዳር 25/2010 ሲሆን ልደታ ፍርድ ቤት መዝገቡን እንዲልክ ሁለት ቀጠሮዎች ተሰጥቶት ነበር። የአማራ ጠቅላይ ፍርድ ቤት በኮ/ል ደመቀ ላይ የቀረበውን ክስና ማስረጃዎች መርምሮ ብይን ለመስጠት ለየካቲት 9/2010 ዓም ቀጠሮ ይዟል።)

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *